Wednesday, July 22, 2015

አባ ገዐርጊ

ግንቦት 18-ጌታችን መልአኩን ልኮ ‹‹ተጋድሎህ በመጠን ይሁን›› በማለት ተጋደሎውን እንዲቀንስ ያዘዘው የአባ ገዐርጊ ዕረፍት ነው፡፡
ጻድቁ የክርስቲያን ወገን ሲሆን ወላጆቹም ደጋግ ቅዱሳን ጻድቃን ናቸው፡፡ በአደገም ጊዜ የወላጆቹን በጎች የሚጠብቅ እረኛ ሆነ፡፡ ነገር ግን እርሱ የምንኩስናን ልብስ ይለብስ ዘንድ በልቡ ይመኝ ነበር፡፡ 14 ዓመትም በሆነው ጊዜ የእግዚአብሔር ጸጋ አነሳሳችውና በጎቹን ትቶ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደ፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣል›› እንዳለው (2ኛ ቆሮ 11፡14) አባ ገዐርጊ ወደ ገዳሙ እየተጓዘ ሳለ በሽማግሌ አምሳል ከይሲ ሰይጣን ተገለጠለትና ከዓላማው ሊያደናቅፈው ፈተነው፡፡ እንዲህም አለው ‹‹ልጄ ሆይ ስለ አንተ አባትህ ልብሱን ቀዶ አየሁት፣ የዱር አውሬ ነጥቆ የበላህ መስሎት አባትህ ያዝናል፣ ያለቅሳል፡፡ ተመልሰህ የአባትህን ልብ ልታጽናና ይገባሃል›› አለው፡፡ አባ ገዐርጊም ደንግጦ አንድ ሰዓት ያህል ሳይንቀሳቀስ ቆመመ፡፡ ከዚህም በኋላ የከበረ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቅዱስ ወንጌሉ ‹‹ከእኔ ይልቅ አባት እናቱን የሚወድ ለእኔ ሊሆን አይባውም ደቀ መዝሙሬም ሊሆን አይችልም›› ብሏል ብሎ አሰበ፡፡ ማቴ 10፡37፡፡ ይህንንም ባሰበ ጊዜ ሰይጣን እንደጢስ ሆኖ ተበትኖ ጠፋ፡፡ አባ ገዐርጊም ሰይጣን እንደሆነ ዐወቀ፡፡ ‹‹በመጠን ኑሩ ንቁም፣ ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና ለእግዚአብሔር ተገዙ፣ ዲያብሎስን ግን ተቃወሙ ከእናንተም ይሸሻል›› 1ኛ ጴጥ 5፡8፣ ያዕ 4፡7፡፡

በዚያን ጊዜም አስቀድሞም ተገልጦለት የነበረው የብርሃን ምሰሶ ተገለጠለት፣ የእግዚአብሔርም መልአክ በመነኩሴ አምሳል ተገለጠለትና አብሮት ተጓዘ፡፡ መልአኩም አባ ገዐርጊን አባ አርዮን ገዳም አደረሰው፡፡ አባ ገዐርጊም ጽኑ ተጋድሎውን ጀመረ፡፡ በገዳሙ 14 ዓመት በታላቅ ተጋድሎ ሲኖር እህል አይቀምስም ውኃም አይጠጣም ነበር፡፡ ለ14 ዓመትም ከመቀመጥ በቀር ምንም አልተኛም፡፡ ከዚህም በላይ ተጋድሎውን በጨመረ ጊዜ እግዚአብሔር መልአኩን ልኮ ‹‹በመጠን ተጋደል›› ብሎታል፡፡ መልአኩም ተገልጦለት ‹‹‹ሥጋህ እንዳይደክም በመካከለኛ ተጋደል› ብሎሃል ጌታ›› ካለው በኋላ ሊሠራው የሚገባውን ሥርዓት ሠራለት፡፡ ሁልጊዜም እስከሚመሽ እንዲጾም፣ ትንሽም እንጀራን እንዲበላ፣ ከእራት ሰዓት እስከ መንፈቀ ሌሊት ስለሥጋው ዕረፍት እንዲተኛ በቀረው ሌሊት እስቲነጋ ተግቶ እንዲጸልይ ሥርዓት ሠራለት፡፡
መልአኩ በሠራለት በዚህ ሥርዓት ብዙ ዘመን ሲጋደል ከኖረ በኋላ በበረሃ ውስጥ ብቻውን ወሊኖር ወዶ በጫካ ውስጥ እየተመላለሰ ሁለት ዓመት ተቀመጠ፡፡ ነገር ግን ጌታችን ተገልጦለት ወደ ቀደመ ቦታው እንመለስ አዘዘው፡፡ ደብሩም ከከበሩ መክሲሞስ ዱማትዮስ ገዳም አጠገብ ነበር፡፡ ወደ ደብሩም በተመለሰ ጊዜ አብርሃም ከተባለ ደገኛ ቅዱስ ጋር ተገናኙና ሁለቱም በጋራ ለመኖር ተስማምተው ወደ አስቄጥስ ገዳም አበ ምኔት ወደ አባ ዮሐንስ ዘንድ ሄዱ፡፡ እርሱም ቦታ ሰጥቷቸው በውስጧ በተጋድሎ መኖር ጀመሩ፡፡ ያችም ቦታ እስከዛሬ ታውቃ ትኖራለች፡፡ ስሟም በግቢግ ትባላለች፡፡ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጣሪያዋን ሰንጥቆ ወደ እነዚህ ሁለቱ ቅዱሳን የወረደባት ናት፡፡ እነርሱም በክብር ሰገዱለት፡፡ ጌታችንም ባርኳቸውና አጽናንቷቸው ዐረገ፡፡ በዚያችም ጌታችን በወረደባት መስኮት ብርሃን ተመለከቱ፡፡ እስከዛሬም ድረስ የተከፈተች ሆና ትታያለች፡፡ እነዚህም ሁለት ቅዱሳን (አባ ገዐርጊና አባ አብርሃም) ለመኮሳት የሚሆኑ ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሱ፡፡ ከዚህም በኋላ አባ አብርሃም ጥር 2 ቀን ዐረፈ፡፡ ከእርሱም በኋላ አባ ገዐርጊ በ72 ዓመቱ ግንቦት 18 ቀን ዐረፈ፡፡
የአቡነ ገዐርጊ ምልጃና በረከቱ በምልጃው በምንታመን በሁላችን ላይ ይደርብን! አሜን!!!
(ምንጭ፦ የግንቦት ወር ስንክሳር)

Tuesday, July 21, 2015

ጩጊ ማርያም- ከጸበሉ ጠጥተው ስጋቸው ያልፈረሰ ፍየሎች

❖❖❖ በስመ ሥላሴ ❖❖❖

እነሆ ጌታ ፈቅዶ የሰማሁትን ያየሁትን እነግራቹ ዘንድ ጀመርኩ የዘንድሮዉን የሰኔ ጎሎጎታ ክብረ በዓል አከብር ዘንድ ወደ ቅዱሱ እና በጌታ ፍቅር በተጠመደዉ እና ከልጅነቱ ጀምሮ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት ፀንቶ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎችን አፍርቶ በፀጋ ከፍ ወዳለዉ የነ አቡነ አምደሥላሴ ወዳጅ ወደነበሩት ወደ አቡነ ምዕመነድንግል ገዳም ነበር የተጓዝኩት ። የኚ አባት ገዳም ልዩ መታወቂያ ስሙ ጩጊ ማርያም በመሰኘት ይታወቃል ። ከጎንደር 25 km ርቀት ያላት ሲሆን ኮሶዬ ከተባለች አካባቢ ሲደርሱ ለበረታ የ2 ሰዓት ለደከመ ከ 2ሰዓት በላይ ሚያሰኬደዉን መንገድ ይጀምራሉ ። አቡነ ምዕመነድንግል እንደ ቀደምት አበዉ ጠንካራ እና ለሃይማኖተ ክርስቶስ ቀናተኛ የነበሩና በዋልድባ ገዳም በአበምኔትነት ያገለገሉ ኀላም ውዳሴ ከንቱን በመሸሽ ከገዳሙ ርቀዉ አሁን ወዳሉበት ብዙ ፅድ እና ወይራ ወዳለባት /ጩጊ / መጥተዋል በዚህ ስፍራ ለረዥም ግዜ ተጋድሎ አርገዉበታል ። በዚህ ስፍራ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከድንግል ማርያምና ከቅዱሳን ሁሉ ጋር ተገልጦ ለአባታችን ቃል ኪዳን ሰጥቶአቸዋል፣ አንዲሁም እንደ ትንሽ ብላቴና አቅፎአቸዉ ስሞአቸዋል ፣እንዲሁም በጌታ አዳኝነት አምነዉ በቅዱሱ አቡነ ምዕመነድንግል ፀሎት ሚታመኑ ሁሉ ፈዉስ ይሆናቸዉ ዘንድ ሁለት ማየ ዮርዳኖስ አፍልቆላቸዋል ከዚ ማየ ዮርዳኖስ የጠጡ ሁሉ ከደዌ ከመፈወሳቸዉ በተጨማሪ በድን ስጋቸዉ አይፈርስም አይበሰብስም ለዚ እንደማሳያ የሚሆኑ 16 ፍየሎች ከዚ ማየ ዮርዳኖስ ጠጥተዉ አሁንም ድረስ ሰዉነታቸዉ ሳይፈርስ አሁንም በሕይወት ያሉ ይመስላሉ ። አባታችን አቡነ ምዕመነድንግል አካሄዳቸዉን በጌታ ቃል እና ትምህርት ስላፀኑ ሞትን ሳያዩ እንደነ ሄኖክ ፣ ኤልያስ ፣ አቡነ አረጋዊ ፣ቅ.ያሬድ ተሰዉረዋል ።  አምላከ አቡነ ምዕመነድንግል እግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ ይማረን ፣ ይባርከን ። አሜን !!

Wednesday, July 1, 2015

ታላቁ ጻድቅ ንጉሥ የዐፄ ካሌብ

ግንቦት 20-ንጽሕናን ከቅድስና ጋር አስተባብሮ በመያዝ እግዚአብሔርንም ሰውንም በቅድስናና በፍቅር ያገለገለው የታላቁ ጻድቅ ንጉሥ የዐፄ ካሌብ ዕረፍት ነው፡፡ እናም ዛሬ በዕረፍቱ ዕለት ገድሉን ትሩፋቱን የቅድስና ሥራውን አብዝተን በመናገር አስበነው እንውላለን፤ በረከቱን እንካፈላለን፡፡ ይኸውም ታላቅ ጻድቅ ንጉሥ ዋጋው እጅግ የከበረውንና በነገሠ ጊዜ በራሱ ላይ የጫነውን የወርቅ ዘውዱን ከጌታችን መካነ መቃብር ላይ ይሰቅልለት ዘንድ ከአደራ ደብዳቤ ጋር ለኢየሩሳሌሙ ሊቀ ጳጳሳት ለአባ ዮሐንስ ከላከለት በኀላ ዓለምን ንቆ፣ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ አንዲት የውኃ መንቀል ብቻ በመያዝ በአባ ጰንጠሌዎን እጅ በመመንኮስ ገዳማቸው አጠገብ ከሚገኝ ዋሻ ውስጥ ገብቶ 12 ዓመት በጾም በጸሎት በብዙ ድካምና ተጋድሎ እግዚአብሔርን ሲያገለግል ኖሮ ዛሬ ግንቦት 20 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፏል፡፡
መልካም የበረከት ንባብ ይሁንልን!!! (የጽሑፉ ምንጭ ገድለ አቡነ አረጋዊ፣ ገድለ አቡነ ጰንጠሌዎንና የኅዳርና የግንቦት ወር ስንክሳር ናቸው)

በቍስጥንጥንያ ዮስጢኖስ በነገሠ በ5ኛው ዓመት ዐፄ ካሌብ በኢትዮጵያ ነግሦ ነበር፡፡ የአይሁድም ንጉሥ ፊንሐስ ነበር፡፡ በዚህም ወቅት ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት የኢየሩሳሌሙ አባ ዮሐንስ፣ የቍስጥንጥንያው አባ ጢሞቴዎስ፣ የእስክንድርያውም አባ ጢሞቴዎስ፣ የአንጾኪያው አባ አውፍራስዮስ ነበሩ፡፡ ሳባ የምትባለው አገር በኢትዮጵያ ነገሥታት እጅ ውስጥ ነበረች፡፡
የሮም ነገሥታት አስባስያኖስና ጥጦስ አይሁድን ወረው አሳደዷቸውና ይህችን ሳባን አይሁድ ወረሷት፡፡ በውስጧም በጌታችን የሚያምኑ ብዙ ሕዝቦች ነበሩባት፡፡ በሳባ ውስጥም ክርስቲያኖች የሚኖሩባት ታላቅ ከተማ ነበረች፡፡ የአይሁድ ንጉሥ ፊንሐስም ወደ ከተማዋ ገብቶ በሺህ የሚቆጠሩትን ክርስቲያኖች ገደለ፡፡ ዙሪያ ዳር ድንበሯ በመስቀል ምልክት የታጠረች ስለነበረች ፊንሐስ መጀመሪያ መግባት ሳይችል ሲቀር ‹‹ወደ ውስጥ ገብቼ የከተማዋን አሠራር፣ ገበያዋን፣ አደባባዮቿን መጎብኝት እሻለሁ እንጂ ክፉ አላስብም፣ የማንንም ደም አላፈስም›› ብሎ ምሎ ወደ ውስጥ ገባ፡፡ ከነሠራዊቱ ከገባ በኋላ ግን መግደል ጀመረ፡፡ መጀመሪያውንም አቡነ ኂሩተ አምላክ ‹‹ውሸቱን ነው አታስገቡት፣ ሐሰተኛ ነው ደጁን ከፍታችሁ አታስገቡት›› ብለው ቢነግሯቸውም የሚሰማቸው ጠፋ፡፡ ፊንሐስም እንደገባ የሕዝቡን ገንዘብ ዘረፈ፤ ቀጥሎም በነልባሉ አየር ላይ ደርሶ እስኪታይ ድረስ እሳት አስነድዶ ‹‹ኤጲስ ቆጶሱን አባ ጳውሎስን አምጡልኝ›› ብሎ አዘዘ፡፡ እንደሞቱም ሲነገረው ዐፅማቸውን ከመቃብር አውጥቶ አቃጠለው፤ ቀጥሎም ቀሳውስትን፣ ካህናትን፣ ዲያቆናትን፣ መነኮሳትን ሁሉ በእሳቱ ውስጥ እንዲጨምሯቸው አዘዘ፡፡ አራት ሺህ ሃያ ሰባት ክርስቲያኖችም ወደ እሳቱ ተጥለው በሰማዕትነት ሞቱ፡፡
ፊንሐስም አቡነ ኂሩተ አምላክንና ታላላቅ መኳንንትን ግን አሳስሮ ብዙ አሠቃያቸው፡፡ ‹‹ክርስቶስን ያልካደ ሁሉ ተሠቃይቶ ይሞታል›› የሚል አዋጅ በከተማው እንዲነገር አዘዘ፡፡ አቡነ ኂሩተ አምላክንም አስሮ እያሠቃያቸው በከተማው አዞራቸው፡፡ ሕዝቡም ጌታችንን አንክድም እያሉ ወጥተው ተገደሉ፡፡ በዚህም ጊዜ የተገደሉት ቁጥራቸው 4252 ሆነ፡፡
የአቡነ አቡነ ኂሩተ አምላክን ሚስት ቅድስት ድማህን ከ2 ልጆቿ ጋር ይዞ አሠቃያቸው፡፡ አንደኛዋም የ12 ዓመት ሕፃን ምራቋን በፊንሐስ ላይ ተፋችበት፣ እርሱም ሰይፉን መዞ አንገቷን ቆረጠው፡፡ ለቅድስት ድማህም የልጇን ደም አጠጣት፡፡ ድማህም ‹‹ይህን እንዲሆን የፈቀደ እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን›› ብላ አምላኳን ስታመሰግን ሰምቷት እናቲቱንም አንገቷን ቆረጠው፡፡ አቡነ ኂሩተ አምላክንም ወደ ውጭ አውጥቶ ‹‹የምታመልኩትን ክርስቶስን ካዱ›› አላቸው፡፡ አቡነ ኂሩተ አምላክም ‹‹ክብር ይባውና ጌታዬን ኢየሱስ ክርስቶስን እያለመኩ ስኖር 78 ዓመት ሆነኝ፣ እስከ አራት ትውልድም ለማየት ደርሻለሁ፡፡ ዛሬም ስለከበረ ስሙ ምስክር ሆኜ ስሞት እጅግ ደስ ይለኛል፡፡ ወደዚህ ለመግባት ስትምል እኔም አስቀድሜ መሐላህን እንዳያምኑ ለወገኖቼ ነግሬአቸው ነበር፤ አንተ ሐሰተኛ ነህና ነገር ግን ይህ ሁሉ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው፤ ለዚህ ተጋድሎ ላበቃኝ ለእርሱ ምስጋና ይሁን›› እያሉ ፊንሐስን በተናገሩት ጊዜ ወደ ወንዝ ወስዶ አንገታቸውን አስቆረጠው፡፡ አቡነ ኂሩተ አምላክም በሰማዕትነት ከማረፋቸው በፊት የኢትዮጵያንና የሮምን መንግሥት ያጸና ዘንድ የአይሁድን መንግሥት ግን ያጠፋ ዘንድ ጌታችንን ለመኑት፡፡ ዕረፍታቸውም ኅዳር 26 ቀን ነው፡፡
አቡነ ኂሩተ አምላክም ሕዝቡን ተሰናብተው በተሰየፉ ጊዜ አንዲት ሴት ደማቸውን ለ5 ዓመቱ ልጇ ቀባችው፡፡ ይህንንም ሲያዩ ልጇን ነጥቀው ለንጉሡ ሰጥተው እርሷን ከእሳቱ ውስጥ ጨመሯት፡፡ ንጉሡ ፊንሐስም ሕፃኑን ‹‹እኔን ትወዳለህ ወይስ ክርስቶስ የሚሉት?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ የ5 ዓመቱ ሕፃንም ‹‹እኔስ የእጁ ሥራ ነኝና ክርስቶስን እወደዋለሁ፣ ይልቅስ ልቀቀኝና ወደ እናቴ ልሂድና ሰማዕትነቴን ልፈጽም›› አለው፡፡ ፊንሐስም ከእጁ እንዳይወጣ በያዘው ጊዜ እግሩን ነክሶት አምልጦት ሮጦ ሄዶ ከእሳቱ ውስጥ ገባ፡፡ ሁለተኛም የ10 ወር ሕፃን የተሸከመች አንዲት አማኝ ሴት ወደ ልጇ እያየች ‹‹ልጄ ሆይ ዛሬስ ላዝንልህ አልቻልኩም›› ብላ ስትናገር በእቅፏ ያለው የ10 ወሩ ሕፃን ልጇም አንደበቱን ከፍቶ ‹‹እናቴ ሆይ በፍጥነት ወደ ዘላለም ሕይወት እንሂድ ይህችን እሳት ከዛሬ በቀር አናያትምና›› አላት፡፡ እርሷም ልጇን ይዛ ዘላ እሳቱ ውስጥ ተወርውራ ገባች፡፡ የክርስቲያን ወገኖችም ይህን ሁሉ አይተው እኩሉ ወደ እሳት እኩሉ ወደ ሰይፍ ተሽቀዳደሙ፡፡ ራሳቸው የአይሁድ ሠራዊት ዕፁብ ብለው እስኪያደንቁ ድረስ ክርስቲያኖቹ ወደ ሰማዕትነት ተፋጠኑ፡፡ ቁጥራቸው ሃያ ሺህ ነበር፡፡ ክርስቲያኖቹም በሚሞቱበት ጊዜ የረዳቶቻቸውን የቊስጥንጥንያንና የኢትዮጵያን ነገሥታት ስም በጸሎታቸው ይጠሩ ነበር፡፡
ከዚህም በኋላ እሳቱ በሰማይ ውስጥ መልቶ 40 ቀንና 40 ሌሊት ታየ፡፡ ፊንሐስም ወደ ሀገሩ በተመለሰ ጊዜ ወደ ነገሥታቱ ሁሉ በኋይሉ እየተመካ ላከባቸው፡፡ የሮሜው ንጉሥ ዮስጢኖስም ይህን ሰምቶ ወደ እስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ ወደ አባ ጢሞቴዎስ መልአክት ላከ፡፡ ለሀገረ ናግራን ክርስቲያኖች ደማቸውን ይበቀልላቸው ዘንድ ለኢትዮጵያው ንጉሥ ለዐፄ ካሌብ መልእክት እንዲልክ ነገረው፡፡ ዐፄ ካሌብም ተጽፎለት መልእክቱ ሲደርሰው ፈጥኖ ተነሣ በዋሻ ከሚኖር ከአቡነ ጰንጠሌዎን በረከትን ተቀብሎ ለአቡነ አረጋዊም በጸሎት እንዲያስቡት ደብዳቤ ጽፎ ከላከ በኋላ ከሠራዊቱ ጋር በመርከብ ተጭኖ ወደ ሀገረ ናግራን ሄደ፡፡
ከመሄዱም በፊት ለአቡነ አረጋዊ የላከላቸው መልእክት እንዲህ የሚል ነው፡- ‹‹ፊንሐስ የተባለ አረማዊ የናግራን ክርስቲያኖችን ደም በከንቱ ያፈሰሰ፣ ቤተክርስቲያንን የመዘበረና ያጠፋ ፍጹም የእግዚአብሔር ጠላት ወደሚሆን ሔጄ እዋጋው ዘንድ ተዘጋጅቻለሁ፡፡ ስለዚህ አባቴ ሆይ! አንተም በበኩልህ ጸሎት አድርግልኝ፣ የጻዲቅ ጸሎት ትራዳለች፣ ኃይልንም ታሰጣለች፣ በጠላት ላይ ድልንም ታቀዳጃለችና›› ሲል ላከበት፡፡
አባታችን አቡነ አረጋዊም ለንጉሡ ጭፍሮች ‹ወደ ጦሩ ግንባር ሒድ፣ እግዚአብሔር ጠላቶችህን ከእግርህ በታች ያስገዛልህ፣ ለአንተም ግርማ ሞገስ ይስጥህ፣ በሰላም ይመልስህ›› ብለው መርቀው ላኩበት፡፡ ከዚህ በኋላ ዐፄ ካሌብ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ ጥሎ ማቅ ለብሶ በፍጹም ልመና ብዙ ጸሎት ካደረገ በኀላ ወደ የመን ሳባ በመርከብ ተጓዘና ከከሐዲው ፊንሐስ ጋር ጦር ገጠመ፡፡ ከሐዲውን ንጉሥ ፊንሐስን ራሱ ዐፄ ካሌብ ገጠመውና በፈረሱ ላይ እንደተቀመጠ በጨበጣ በጦር ወግቶ ገደለውና ወደ ባሕር ገልብጦ ጣለው፡፡
ከዚያም ዐፄ ካሌብ ዛፋር ወደምትባለው ከተማ ሔዶ እርሷንም ተቆጣጠራት፡፡ በእዚያም ያሉ የፊንሐስን ሹማምንቶች እያፈላለገ በአደባባይ እንዲገደሉ በማድረግ የክርስቲያኖቹን ደም በሚገባ ተበቀለ፡፡ የናግራንንም ሕንፃዎቿዋን አደሰ፤ የሰማዕታቱንም መታሰቢያ አቆመ፡፡ ወደ እስክንድርያው አባ ጢሞቴዎስና ወደ ሮሜው ንጉሥ ዮስጢኖስም የድል መልእክት ላከላቸውና እነርሱም ሰምተው እጅግ ተደሰቱ፡፡ በአንጾኪያ፣ በእስክንድሪያ፣ በሮም፣ በቊስጥንጥንያና በዓለም ላይ ያሉ ክርስቲያኖች ሁሉ ይህን ሲሰሙ በእጅጉ ተደሰቱ፡፡ ይህም የሆነው በ525 ዓ.ም ነው፡፡ ጠፍተው የሔዱ ክርስቲያኖችንም ሰበሰባቸውና ወደቀደመ ቦታቸው መለሳቸው፣ ቤተክርስቲያናቸውን አነጸላቸው፡፡ ከሳባ ሀገር የማረከውን ንብረት ሁሉ ለቤተክርስቲያን ሰጥቶ ዓሥር ሺህ ጠባቂ ሠራዊት ሰቷቸው ወደ አክሱም በሰላምና በፍጹም ደስታ ተመለሰ፡፡
ንጉሡ ዐፄ ካሌብ የናግራን ሰማዕታት ደም ተበቅሎላቸው ሁሉንም ነገር አስተካክሎላቸው በደስታ ወደ አክሱም ከተመለሰ በኋላ ‹‹ይህን ያደረገልኝን አምላኬን በምን ላስደስተው?›› ሲል አሰበና ተድላውን፣ ደስታውን ዓለምን ንቆ፣ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ አንዲት የውኃ መንቀልና አንዲት ምንጣፍ ብቻ ይዞ አባ ጰንጠሌዎን ገዳም አጠገብ ከሚገኝ ዋሻ ውስጥ ገብቶ በአባ ጰንጠሌዎን እጅ መንኩሶ ለመቀመጥ ወሰነ፡፡ አባ ጰንጠሌዎንንም ‹‹አመንኩሰኝ›› አላቸውና የመላእክትን አስኬማ አልብሰው አመነኮሱት፡፡ ዐፄ ካሌብም ዳግመኛ ከዋሻው ወጥቶ ዓለምን በዐይኑ እንዳያይ ማለ፡፡ ዋጋው እጅግ የከበረውንና በነገሠ ጊዜ የጫነውን ዘውዱን ከጌታችን መካነ መቃብር ወይም በር ላይ ይሰቅልለት ዘንድ ከአደራ ደብዳቤ ጋር ለኢየሩሳሌሙ ሊቀ ጳጳሳት ለአባ ዮሐንስ ላከለት፡፡ ዳግመኛም ንጉሡ ዐፄ ካሌብ ‹‹አባቴ ሆይ በአንተ ጸሎት በእግዚአብሔር ቸርነት ከጦርነቱ በሰላም ተመልሻለሁ፤ አሁንም የክርስቶስን አርዑተ መስቀል ተሸክሜአለሁና እግዚአብሔር ለፍጻሜው ያብቃህ እያልህ ስለ እኔ ጸልይልኝ›› ብሎ ወደ አባታቸን ወደ አቡነ አረጋዊ ላከበት፡፡ ስለዚህም ነገር አቡነ አረጋዊ በጣም ተደሰቶ ‹‹ልጄ ሆይ! መልካሙንና የበለጠውን አድርገሃል፣ አሁንም እግዚአብሔር የፈቀደከውን ነገር ሁሉ ይፈጽምልህ›› ብለው መረቁት፡፡ ኢትዮጵያዊው ንጉሥ ዐፄ ካሌብ ይህን ዓለም በመናቅ በበረሃ በዋሻ 12 ዓመት በጾም በጸሎት በብዙ ተጋድሎ ከኖረ በኋላ ግንቦት 20 ቀን ዐርፎ እስከ ዘለዓለሙ ድረስ የማያልፍ ሰማያዊ ክብርን ወርሷል፡፡ መካነ መቃብሩም አክሱም በአባ ጰንጠሌዎን ገዳም ምድር ቤቱ ውስጥ ይገኛል፡፡
ይኸውም አባ ጰንጠሌዎን ከተሰዓቱ ቅዱሳን ውስጥ አንዱ ሲሆን በገዳሙ ውስጥ ሳይቀመጥ ሳይተኛ በእግሩ ቆሞ 45 ዓመት የጸለየ የበረከት አባት ነው፡፡ ምድራዊ ወይም ሥጋዊ የሆኑ ፍትወታት ፈጽመው ጠፍተውለታልና ከመላእክትም ማኅበር ጋር አንድ ሆኗልና ከፍጹም ምስጋና በቀር እህል ወይም ውኃ ወይም ቅጠል እንኳ አይቀምስም ውኃም አይጠጣም ነበር፡፡ እርሱም የንጉሥ ልጅ ስለነበር አስቀድሞ ንግሥናን ንቆ የመነነ ነው፡፡ የመንፈስ ወንድሞቹም እንዲሁ፡፡
እነዚህም ተሰዓቱ ቅዱሳን ሁሉም የነገሥታት ልጆች ሲሆኑ በዓለም ነግሠው መኖርን እርግፍ አድርገው ትተው ከያሉበት ከቁስጥንጥንያ፣ ከአንጾኪያ፣ ከግሪክ፣ ከእስያ፣ ከሮምያና ከቂሣርያ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በአንድነት ተሰባስበው በአባ ጳኩሚስ ገዳም ገብተው በምንኩስና ሲኖሩ ኢትዮጵያ በሃይማኖት በምግባር ያጌጠች ቅድስት ሀገር መሆኗን ሲሰሙ ‹‹ይህችንማ ሄደን ማየት አለብን›› ተባበብለው ያላቸውን ሁሉ ይዘው ታቦቶቻቸውን፣ ካህናቶቻቸውን፣ ንዋየ ቅድሳቶቻቸውን፣ መጻሕፍቶቻቸውን ሁሉ ይዘው በዘሚካኤል (አቡነ አረጋዊ) መሪነት በመምጣት በ460 ዓ.ም ጳጳሱና ንጉሡ ካሉበት አክሱም ከተማ ገቡ፡፡
በዚያም ለ12 ዓመታት በፍጹም አንድነት አብረው ከተቀመጡ በኋላ ‹‹እርስ በራሳችን እየተያየን ብንኖር ተድላ ደስታ ይሆንብናልና ተለያይተን እንቀመጥ›› ብለው ተማከረው በተለያየ በዓት በተጋድሎ መኖር ጀመሩ፡፡ አባ ሊቃኖስ በደብረ ቁናጽል፣ አባ ጰንጠሌዎንም በእርሱ ትይዩ በሆነ ቦታ፣ አባ ገሪማ በደብረ መደራ፣ አባ ጽሕማ በደብረ ጸድያ፣ አባ ይምአታ በደብረ ገረዓልታ፣ አባ አፍጼ በደብረ ይሐ፣ አባ አሌፍ በደብረ አኅድአ መኖር ጀመሩ፡፡ አባ አረጋዊ ደግሞ በጣም ርቀው በመሄድ በደብረ ዳሞ በዋሻና በፍርኩታ ውስጥ በተራራም ላይ መኖር ጀመሩ፡፡
ተሰዓቱ ቅዱሳን ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን ያደረጉ ነበር፣ ተአምራቶቻቸውን መንፈሳዊ ዐይኑ ያልበራለት ሰው ከቶ ሊረዳውና ለገነዘበው አይችልም፡፡ መላእክትም ዘወትር ባለመለየት ይጎበኙዋቸው ነበር፡፡ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስም ዘወትር እየተገለጠላቸው ይባርካቸውና ቃልኪዳን ይሰጣቸው ነበር፡፡ በጸሎታቸውም አጋንንትን ያስወጣሉ፣ ድውያንን ይፈውሳሉ፣ ዕውራንን ያበራሉ፣ ሙታንን ያስነሣሉ፡፡ ለእያንዳንዳቸውም የሃይማኖታቸውን ኃይል አሳዩ፡፡ ከእነርሱ መካከል ተራራ ያፈለሱ አሉ፣ ባሕሩን ከፍለው ደረቅ መንገድ ያደረጉ አሉ፣ ጠዋት ዘርተው ማታ ሰብስበው የሚያጭዱ አሉ፣ ይኸውም የስንዴውን ነዶ በግራር ዛፍ ላይ አበራይተው የዛፉ ቅጠል ሳይረግፍ በሬዎቹም ከዛፉ ላይ ሳይወድቁ ምርቱ ብቻ እየወረደ በአውድማው ላይ እንዲከማች ያደረጉ አሉ፣ ወዲያውም ስንዴውን ለመገበሪያ ሠይመው ለዘጠኝ ሰዓት መሥዋዕተ ቊርባን ያደረሱ አሉ፡፡
በዓለት ድንጋይ ላይ የወይራ ተክል ተክለው በዚያኑ ጊዜ ጸድቆ ለምልሞ ታላቅ ዛፍ ከሆነ በኋላ በእግዚአብሔር ፈቃድ ግንዱ ደርቆ ቆርጠውና ፈልጠው እንጨቱን አንድደው እሳቱ ፍም ከወጣው በኋላ ፍሙን በቀጭን ሻሽ ወስደው ለዘጠኝ ሰዓት የቅዳሴ ማዕጠንት ያደረሱ አሉ፡፡ ለቤተክርስቲያን አገልግሎት የሚውልና ለሥርዓተ ቊርባን ማከናወኛ የሚሆን ውኃው ሳይፈስ በወንፊት ውኃ የሚቀዱ አሉ፡፡
ከእነሱም አንዱ በዐረፈ ጊዜ የሥጋው ሥርዓተ ግንዘት በመላእክት እጅ የተከናወነ አለ፡፡ ይልቁንም ቁመቱና ርዝመቱ ከታላላቅ ገደል እጅግ በጣም የሚበልጥ የድንጋይ ዓምድ ከወንዝ ማዶ ዘንበል ብሎ መጥቶ ሥጋቸውን በክብር ተቀብሎ በተራራው ጫፍ ላይ እስከዛሬም ድረስ ፈጽሞ ሳይነቃነቅና ሳይናወፅ ቀጥ ብሎ ቆሞ ይገኛል፡፡ የሰዎቹም የመግነዝ ምልክት ጥበበኛ እንደሣለው ሥዕል በድንጋዩ ዓምድ ላይ ተስሎ ወይም ተቀርፆ ይታያል፡፡ ቆመው ጸሎት በሚጸልዩበት ጊዜ ዓሥሩ የእጆቻቸው ጣቶችና ዓሥሩ የእግሮቻቸው ጣቶች እንደፋና የሚያበሩበትና እንደመብረቅ የሚብለጨልጩበት ጊዜ አለ፡፡
ሀገራችን ኢትዮጵያ ያለአንዳች ሐዋርያ ስብከት አስቀድማ በክርስቶስ እንዳመነችና በዚህም ምክንያት የልዕልናዋን ታሪክ ለዓለም ለማሳወቅ ፈጥነው የሄዱ አሉ፡፡ የኢትዮጵያ ምድር በእነዚህ የቅዱሳን ኪደተ እግር ተቀደሰች፣ በውስጧም በመመላለሳቸው አውራጃዎቿና አደባባዮቿ ሁሉ ታደሱ፡፡ መዓዛ ትምህርታቸውና ተአምራቶቻቸው በሁሉም አውራጃዎች ተሠራጨ፣ የእምነቷንም መሠረት አጸኑ፡፡
የቅዱሳኑ ምልጃቸውና በረከታቸው በአማላጅነታቸው በምንታመን በሁላችን ላይ ይደርብን! አሜን!!!

ገድለ ቅዱሳን

ግንቦት 19 ዕለት ታስበው የሚውሉ 6 ታላላቅ ዓመታዊ በዓላት አሉ፡፡
፩. ጌታችን 5 ጊዜ ከሞት እያስነሣውና ስለ ስሙ ምስክር የሆነለት የ12 ዓመቱ ሕጻን የቅዱስ ኤስድሮስ ዕረፍት ነው
፪. በወሎ ላስታ ሰውንና ዝንጀሮን በቃልኪዳን ያስተሳሰሩት እና እመቤታችን ዕጣን እየሰጠቻቸው ከ24ቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥላሴን መንበር ያጠኑት የአቡነ ዮሴፍ ዘእጂፋት ዕረፍት ነው
፫. ዳግመኛም ጌታችን ነገልጦ ‹‹ለእናቴ ዓሥራት የሰጠኋት፣ ለወዳጄ ለጊዮርጊስ፣ ለባለሟሌ ለገብረ መንፈስ ቅዱስ ዓሥራት የሰጠኋት ይህችን ቅድስት ሀገር ያሬድንና ጊዮርጊስን ያፈራችውን ኢትዮጵያን በጸሎትህ ጠብቅ›› ብሎ ያዘዛቸው የአቡነ ዮሴፍ ዘአክሱም ዕረፍት ነው
፬. ስመ እግዚአብሔር ሲጠራባቸው ስለ ስሙ ሲሉ ራሳቸውን ለሞት አሳልፈው የሰጡት በጸሎታቸውም ውኃውን ደም ያደረጉት የአቡነ ዓቢየ እግዚእ ዕረፍት ነው
፭. ጸሎታቸውን ሲጀምሩ ሰማያት ተከፍተው የመላእክትን አገልግሎት በግልጽ የሚያዩት እና ሰይጣን ለመጀመሪያ ጊዜ ከጳውሎስ ሳምሳጢን ጀምሮ እስከ ንስጥሮስንና ልዮን ድረስ ያስተማራትን የክህደት ት/ት ከሀገራችን ያጠፉልን የአቡነ ብስጣውሮስ ዘሐይቅ ዕረፍት ነው
፮. ዳግመኛም ቤተ መቅደሱን በባሕር ላይ የሠራውና በምድራዊ ስንዴና ወይን ያይደለ መላእክት ሰማያዊ ኅብስትና ጽዋ እያመጡለት 22 ዓመት ሥጋ ወደሙን ሰፈትት የኖረው የጻድቁ ንጉሥና ካህን የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ልደት ነው፡፡ 

የእነዚህን ቅዱሳን የሁሉንም ሙሉ ገድላቸውን በዝርዝር በደንብ እንመለከታለን በእርጋታ ሆናችሁ በተመስጦ አንብቡት፡፡ መልካም የበረከት ንባብ ይሁንልን!!! 

የጽሑፉ ምንጮች፡-
፩. ገድለ አቡነ ብስጣውሮስ ዘሐይቅ
፪. ገድለ አቡነ ዓቢየ እግዚእ
፫. ገድለ ቅዱስ ላሊበላ
፬. ገድለ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ
፭. ገድለ ቅዱስ ቂርቆስ ወኢየሉጣ
፮. ስንክሳር ዘወርሃ ግንቦት
፯. የቅዱሳን ታሪክ-107፣140
፰. መዝገበ ታሪክ ናቸው፡፡

ሕጻኑ ሰማዕት ቅዱስ ኤስድሮስ፡- ሀገሩ እስክንድርያ ሲሆን አባቱ በድላዖን እናቱ ሶፍያ ከቤተ መንግሥት ወገኖች ናቸው፡፡ አባቱ የዲዮቅልጥያኖስ መኰንን ነበር፡፡ ከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ በክርስቲያኖች ላይ እጅግ አሠቃቂ መከራ ባደረሰ ጊዜ አባቱ በድላዖን ምስፍናውን ትቶ ሚስቱንና ልጆቹን ይዞ ገዳም ገባ፡፡ ዲዮቅልጥያኖስም ጭፍሮቹን ልኮ አስመጣውና እምነቱን እንዲክድ ጠየቀው፡፡ በድላዖንም ‹‹ክርስቶስን በተውከው ሰዓት እኔም አንተን ተውኩህ›› አለው፡፡ ወዲያም አንገቱን በሰይፍ አስቆረጠው፡፡ ቅዱስ ኤስድሮስ የ12 ዓመት ሕፃን ልጅ ነበርና ይመለስ ይሆናል በሚል በእሥር ቤት እንዲቆይ ተደረገ፡፡ በማግሥቱም ‹‹ክርስትናህን ትተህ የንጉሡን ሃይማኖት ተቀበል›› ብለው ሲያባብሉት እምቢ ቢላቸው በንጉሡ ፊት አቅርበው ደሙ እንደ ውኃ እስኪወርድ ድረስ አሠቃቂ ግርፋትን ገረፉት፡፡ እናቱ ሶፍያም የሕፃኑን ልጇን ደም በዲዮቅልጥያኖስ ፊት ላይ እረጭታ እረገመችው፡፡ ዲዮቅልጥያኖስም በንዴት ከሴት ልጇ ጋር ከወገባቸው ላይ ከሁለት አስቆረጣቸውና ሰማዕትነታቸውን ፈጸሙ፡፡
ቅዱስ ኤስድሮስም ተሰቅሎ ሳለ በእናቱና በእኅቱ የሆነውን ነገር ይመለከት ነበር፡፡ ሆዱን ሰንጥቀው በመቅደድ አንጀቱን አውጥተው ወስደው በተራራ ላይ ጣሉት፡፡ ጌታችንም ከሞት አሥተነስቶት እንደ ቀድሞው ሕያውና ፍጹም ጤነኛ አደረገው፡፡ ኤስድሮስም ተመልሶ ሄዶ ከከሃዲው ንጉሥ ፊት ቆመ፡፡ አሁንም በብረት አልጋ ላይ አስተኝተው ከሥር እሳት አነደዱበት፡፡ ሁለተኛም በብረት ላይ አስተኝተው ፈጩት፡፡ ጌታችንም አስነሣው፡፡ ብዙዎችም በኤስድሮስ አምላክ አመኑ፡፡ ዳግመኛም በእርሱ አምላክ ካመኑት ከ800 ነፍሳት ጋር ሰቀሉት፡፡ አሁን ጌታችን አድኖ አሥነሳው፡፡ በሥቃይም ብዛት አልሞት ቢላቸው አንገቱን በሰይፍ ቆረጡት ነገር ግን አሁንም ለ3ኛ ጊዜ ከሞት አሥነሣው፡፡
ትልቅ ድንጋይ በአንገቱ ላይ አስረው ወደ ባሕር ጣሉት፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም ከባሕሩ ውስጥ አውጥቶ በንጉሡ ፊት አቆመው፡፡ ዳግመኛም ወደ ከተማም ወስዶ ሰቅሎ ገደለው፣ ጌታችንም ለ4 ጊዜ አሥነሣው፡፡ ለተራቡ አንበሶች ሲሰጡት እነርሱም ምንም ሳይነኩት ቀሩ ይልቁንም አክብረው ሲሰግዱለት ቢመለከቱ በንዴት ሰውነቱን ቆራርጠው ወደ ባሕር ጣሉት፡፡ ጌታችንም ከቅዱስ ሚካኤልና ከቅዱስ ገብርኤል ጋር ተገልጦለት ለ5ኛ ጊዜ ከሞት አሥነሣው፡፡ ንጉሡም እጅግ አፈረና የሚያደርገው ቢያጣ በግዞት ወደ ሰሎንቅያ ሀገር ላከው፡፡ በዚያም ብዙ ካሠቃዩት በኋላ ወደ ንጉሡ መለሱት፡፡ ንጉሡም በእሥር ቤት በርሀብ እንዲሠቃይ አደረገው፡፡ በመጨረሻም ቅዱስ ኤስድሮስ ግንቦት 19 ቀን የሰማዕትነት ፍጻሜው ሆነና ተሰቅሎ ዐረፈ፡፡ የኖረበት ዘመን 12 ዓመት ነው፡፡ በቅዱስ ኤስድሮስ ምክንያት በጌታችን አምነው ከኤስድሮስ ጋር አብረው በሰማዕትነት የሞቱት ሰዎች ብዛት ከ8 መቶ ሺህ በላይ ናቸው፡፡ ጌታችን ለሕፃኑ ሰማዕት ለቅዱስ ኤስድሮስ አስደናቂ ቃል ኪዳን ገብቶለታል፡፡
አቡነ ዮሴፍ ዘእንጂፋት፡- ተአምረኛው ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ዮሴፍ ዘእንጂፋት አባታቸው ንጉሡ ዐፄ ዳዊት እናታቸው ዳግም ሞገሳ ይባላሉ፡፡ ትውልድ ሀገራቸው ወሎ መቄት እንጂፋ ነው፡፡ ሲወለዱ በርካታ ሙታን ተነሥተዋል፡፡ ጻድቁ ያላዩት የቅዱሳን ቦታ ያልተሳለሙት ገዳም የለም፡፡ በወሎ ላስታ ሰውንና ዝንጀሮን በቃልኪዳን ያስተሳሰሩ ታላቅ አባት ናቸው፡፡
ከዕለታት በአንዱ ቀን ዝንጀሮዎቹ ተሰብስበው መጥተው እጅ ነሷቸው፡፡ አቡነ ዮሴፍም ጌታችንን ‹‹ምን አበላቸዋለሁ?›› ብለው በጸሎት ጠየቁ፡፡ ጌታችንም ‹‹አንተን ያጅቡ፣ ቅጠሉን ቃርሚያውን ይብሉ›› ብሎ አዘዛቸው፡፡ ዝንጀሮዎቹም ጻድቁን ተከትለው ይጓዙ ጀመር፡፡ አንድ ቀን በመንገድ አብረው ሲሄዱ ዝንጀሮዎቹ ‹‹ራበን›› ብለው ለአባታቸን ቢነግሯቸው ድንጋዩን በጸሎታቸው ባርከው ምግባቸው አድርገው መግበዋቸዋል፡፡ አሁንም ድረስ ላስታ ውስጥ በሚገኘው በጻድቁ ገዳም አካባቢ እህሉ በሚትረፈረፍበት ቦታ ዝንጀሮዎች በብዛት ይገኛሉ፡፡ ዝንጀሮዎቹ የሰውን እህል እንዳይበሉ፣ ገበሬውም ቃርሚያውን እንዳያነሳ በአቡነ ዮሴፍ ቃልኪዳንና ግዝት ተይዘዋል፡፡ በዚህም መሠረት አሁንም ድረስ ዝንጀሮዎቹም የሰውን እህል አይበሉም፣ ገበሬውም ቃርሚያውን አያነሳም፡፡ ገበሬው ቃርሚያውን ቢያነሳ ግን ዝንጀሮዎቹ የእሱን እህል ብቻ ለይተው ይበሉበታል፡፡
በአካባቢው አደገኛና መርዛማ እባቦች በብዛት ቢኖሩም በጻድቁ የገዳሙ ክልል ውስጥ ግን በፍጹም ሰውን አይነኩም፡፡ አቡነ ዮሴፍ ለ40 ቀን ከሰው ጋር ሳይገናኙ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም በደመና እየተመላለሱ ጸሎት ያደርጉ ነበር፡፡ አባታችን የተለያዩ ተአምራትን እያደረጉ ባሕር ከፍለው እየተሻገሩ ሙታንን እያስነሱ ወንጌልን ዞረው አስተምረዋል፡፡ ወደ ሰማይም ተነጥቀው እመቤታችን ዕጣን ሰጥታቸው ከ24ቱ ካህናት ጋር አጥነዋል፡፡ ጻድቁ ያመነኮሷቸው መነኮሳት በጣም በርካታ ናቸው፡፡ አቡነ ዮሴፍ ከብዙ ተጋድሏቸው በኋላ ቃልኪዳን ተቀብለው በመጨረሻ ግንቦት 19 ቀን በክብር ዐርፈው በዚያው በገዳማቸው ተቀብረዋል፡፡
አቡነ ዮሴፍ ዘአክሱም፡- የአቡነ ዮሴፍ ዘአክሱም ልደታቸውና ዕረፍታቸው በተመሳሳይ ግንቦት 19 ቀን ነው፡፡ ልጅ ሆነው እየተጫወቱ ሳለ መልአክ መጥቶ ለወላጆቻቸው የዓለም ሰው እንዳልሆነ ስለነገራቸው ወስደው ለሊቀ ጳጳሱ ሰጧቸው፡፡ በአክሱም ሲማሩ አድገው በ22 ዓመታቸው መንኩሰዋል፡፡ አንጋፋ ከተባሉት የኢትዮጵያ ቅዱሳን አንዱና ዋነኛው ናቸው፡፡
ጻድቁ በጸሎት ላይ እንዳሉ ጌታችን ተገልጦላቸው እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹ትወደኛለህን?›› ብሎ ሲጠይቃቸው ‹‹ጌታዬ ባለወድህማ ኖሮ መች ዓለምን ንቄ እከተልህና ገዳም እገባ ነበር›› አሉት፡፡ ቀጥሎም ጌታችን ‹‹ከወደድከኝስ ለእናቴ ዓሥራት የሰጠኋት፣ ለወዳጄ ለጊዮርጊስ ዓሥራት የሰጠኋት፣ ለባለሟሌ ለገብረ መንፈስ ቅዱስ ዓሥራት የሰጠኋት ይህችን ቅድስት ሀገር ያሬድንና ጊዮርጊስን ያፈራችውን ኢትዮጵያን ጠብቅ›› ብሏቸው ተሰወረ፡፡ ጻድቁም ጌታችን ይህን ከነገራቸው በኋላ እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ ስለ ሀገራችን ቆመው ጸልየዋል፡፡ ሸዋ ቡልጋ ፈጠጋር ውስጥ ለሚገኙት ወንድማቸው ለታላቁ ጻድቅ ለአቡነ ዘካርያስም ስለ ኢትዮጵያ አብዝተው እንዲጸልዩ መልእክት ስለላኩባቸው አቡነ ዘካርያስም ዕድሜ ልካቸውን የጸለዩአት ጸሎት ‹‹የኢትዮጵያን ሕዝብ ማር›› የምትል ነበረች፡፡ የአቡነ ዘካርያስ ገዳም ቡልጋ ውስጥ ይገኛል፡፡ አቡነ ዮሴፍ ዘአክሱም የሀገራችንን ሊቃውንትና ሕዝቡንም ለብቻ ሰብስበው የሮማውያን የሀሰት ትምህርት ነፍስን ለሲኦል የሚዳርግ ፍጹም ክህደት መሆኑን አጥብቀው አስተምረዋል፡፡ ጻድቁ በአንድ ወቅት ርሀብ በሆነ ጊዜ የገዳሙን ድንጋዮች ባርከው ዳቦ አድርገው ሕዝቡን የመገቡ ታላቅ አባት ናቸው፡፡
አቡነ ብስጣውሮስ ዘሐይቅ፡- ሙሉ ስማቸው ዓቃቤ ሰዓት አቡነ ብስጣውሮስ ተብለው የሚጠሩ ሲሆን የትውልድ ሀገራቸው መቅደላ ነው፡፡ አባታቸው ፍተ ድንግል እናታቸው ጽዮን ሞገሳ የሚባሉ ደጋግ ቅዱሳን ናቸው፡፡ አቡነ ብስጣውሮስ በ17ኛው ምእት ዓመት የነበሩ ታላቅ ጻድቅ ሲሆኑ የታላቁና የጥንታዊው ትምህርት ቤትና የሥርዓተ ገዳም ተቋም የደብረ ሐይቅ ቅዱስ እስጢፋኖስ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ገዳም አበምኔት ነበሩ፡፡ በልጅነታቸው ትምህርት ቤት ገብተው የሐዋርያትን ሥርዓትና የቅዱሳት መጻሕፍትን ትርጓሜ በሚገባ ተምረዋል፡፡
በዘመናቸው የሃይማኖት ስደት ስለነበር አባታቸው ፍተ ድንግል ስለ ሃይማኖታቸው በዐላውያን ሰማዕት ሆነው ሲገደሉ አቡነ ብስጣውሮስ የአባታቸውን ዐፅም ይዘው በመሸሽ ወደ ላስታ ሄደው በእመቤታችን ስም በተሠራች ገዳም በደብረ ዠመዶ ወስደው ቀበሯቸው፡፡ በኋላ በዐፄ ፋሲል ዘመን ሃይማኖት ሲመለስ ዐፅማቸውን አፍልሰው አምጥተው አገራቸው ቀብረዋቸዋል፡፡ ከዚህም በኋላ እናታቸው በግድ ሚስት አጭተውላቸው የነበረ ቢሆንም ብዙ ሳይቆዩ ሚስታቸው ስለሞተች ቀድሞም የተመኙትን የምንኩስና ሕይወት ለመኖር ወኑ፡፡ አንድ ቀን አንዱ የደብረ ሐይቅ መነኩሴ የገዳሙን ምርት ገበያ ለመሸጥ ይዘው እንደሄዱ አንድ ቀማኛ ወንበዴ አግኝቶ ሊቀማቸው ሲል አቡነ ብስጣውሮስ ደርሰው አዳኑት፡፡ መነኩሴውንም ወደ ቤታቸው ወስደው በመልካም መስተንግዶ አሳደሯቸው፡፡ መነኩሴውም በዚያች ሌሊት ስለ አቡነ ብስጣውሮስ ብዙ ነገር ከተመለከቱ በኋላ አቡነ ብስጣውሮስን ስለ ምንኩስና አስተማሯቸው፡፡ መነኩሴው በማግስቱ ሲሄዱ ወደ ሐይቅ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ገዳም መጥተው እንዲጎበኟቸውና እንዲባረኩ ነግረዋቸው ሄዱ፡፡ አቡነ ብስጣውሮስም እግዚአብሔር መንገዳቸውን ይመራቸው ዘንድ ብዙ ከጸለዩ በኋላ ወደ ሐይቅ ገዳም ገቡ፡፡ በገበያ ያገኘውና በቤቱ ያሳደረውም መነኩሴ ሲያያቸው ደስ ተሰኝነቶ የገዳሙ አበምኔት ዓቃቤ ሰዓት አባ ዘወልደ ክርስቶስ ዘንድ ወሰዳቸው፡፡ አበምነቱም አቡነ ብስጣውሮስን ገና እንዳዩአቸው ጸጋ እግዚአብሔር እንዳደረባቸው አይተው በጣም ደስ ተሰኙ፡፡ አቡነ ብስጣውሮስም መመንኮስ እንደሚፈልጉ ለአበምኔቱ ሲነግሯቸው አበምኔቱ ‹‹የምንኩስና ሥራ ቀላል አይምሰልህ፣ ብዙዎች ወደ እኛ መጡ ነገር ግን መታገስ ተስኗቸዋል…›› በማለት የምንኩስና ሕይወት ከባድ ፈተና እንዳለበት ነገሯቸው፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ብስጣውሮስም ‹‹በልዩ ልዩ ዓይነት ፈተናዎች ፈትኑኝና ሥራዬን ካዩ በኋላ ያመነኩሱኛል›› አሏቸው፡፡ ከዚህም በኋላ አቡነ ብስጣውሮስ በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደት እየተጋደሉ ገዳሙን በጉልበት ሥራ ብዙ ካገለገሉ በኋላ ከገዳሙ አበምኔት ከዓቃቤ ሰዓት አባ ዘወልደ ክርስቶስ እጅ ምንኩስናን ተቀበሉ፡፡ ተጋድሎአቸውንም ከበፊቱ ይበልጥ በማብዛት መኖር ጀመሩ፡፡
እናታቸው የልጃቸውን መመንኮስ ሰምተው ወደ ሐይቅ መጡ ነገር ግን አቡነ ብስጣውሮስ እናታቸውን ወጥተው ላለማየት ተሠወሩ፡፡ አበምኔቱም በብዙ ፍለጋ አግኘተዋቸው ‹‹ልጄ እናትህ አንተን ለማየት ከሩቅ ሀገር መጥታለችና ሄደህ አግኛት›› ሲሏቸው አቡነ ብስጣውሮስም ‹‹አባቴ ሆይ ጌታችን በወንጌል ያለውን አያስታውሱምን? ‹እነሆ እናትና ወንድሞችህ በውጭ ቆመዋል ባሉት ጊዜ ጌታችን በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ ከሚፈጽም በቀር እናቴ ማን ናት? ወንድሞቼስ እነማን ናቸው?› ብሎ ተናግሮ የለምን? ስለዚህ ወደ እናቴ አልሄድም›› ብለው ለአበምኔቱ መለሱላቸው፡፡ አበምንቱም ‹‹ከመንገዱ ርቀት የተነሣ እናትህ በብዙ ድካም መጥታለችና ልታያት ይገባል›› ብለው ግድ አሏቸው፡፡ አቡነ ብስጣውሮስም ሄደው እናታቸውን ካገኟቸው በኋላ እናታቸውም በዛው መንኩሰው በባሕሩ ዙሪያ ካለው ከሴቶች ገዳም ገብተው ማገልገል ጀመሩ፡፡
አቡነ ብስጣውሮስ ከመልካም የጉልበት ሥራ ጋር ቀን ቀን የዳዊትን መዝመር፣ የነቢያትን መጻሕፍትና መኅልየ መኅልይን ሲደግሙ ይውላሉ ሌሊት ሌሊት ሐይቁ ውስጥ ገብተው እጅግ አብዝተው ሲጸልዩ የብርሃን ዓምድ ተተክሎ ይታይ ነበር፡፡ ጸሎታቸውንም ሲጀምሩ ሰማያት ይከፈቱ ነበር፡፡ ቅዱሳን መላእክትንም ሲወጡ ሲወርዱ ያዩአቸዋል፡፡ አቡነ ብስጣውሮስ በእንደዚህ ዓይነቱ ተጋድሎ ብዙ ሲያገለግሉ ዜና ትሩፋታቸው በሁሉ ዘንድ በዓለም ተሰማ፡፡ አስተዳዳሪው ዓቃቤ ሰዓቱ አቡነ ዘወልደ ክርስቶስም እርጅና ሲጫናቸው ማኅበሩን ሰብስበው ‹‹በእኔ ቦታ አባት የሚሆናችሁን ምረጡ›› አሏቸው፡፡ እነርሱም ‹‹እግዚአብሔር ያመለከተህን አንተ ሹምልን›› አሏቸው፡፡ አባ ዘወልደ ክርስቶስም በጸሎት ከጠየቁ በኋላ ‹‹እግዚአብሔርና እኔ አባት ይሆኑላችሁ ዘንድ አቡነ ብስጣውሮስን መርጠንላችኋል›› አሏቸው፡፡ ቀጥሎ አበምኔቱ ስለ አቡነ ብስጣውሮስ እንዲህ በማለት ትንቢት ተናገሩ፡- ‹‹እርሱ ሃይማኖቱ የቀና ምግባሩ ያማረ በተጋድሎም የጸና በጸሎቱ ሀገርን ይጠብቃል፣ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን በነገሥታቱና በመኳንንቱ ፊት ያደርጋል›› እያሉ ለማኅበሩ በነገሯቸው ጊዜ እጅግ ደስ ተሰኙ፡፡ አቡነ ብስጣውሮስ ግን ይህን ሲሰሙ የመረረ ልቅሶን አለቀሱ፤ ከእነርሱም ዘንድ ይሸሹ ዘንድ ወጥተው በመርከብ ተጭነው ሄዱ፡፡ ነገር ግን ደርሰው ይዘው በእግዚአብሔር ፈቃድ ይሾሟቸው ዘንድ ይዘው አሰሯቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ከሰማይ ‹‹ብስጣውሮስ የአባትህን የአበምኔቱን ቃል አታስተሐቅር›› የሚል ቃል ተሰማ፡፡ ማኅበሩም ይህንን ከሰማይ የመጣውን ቃል በሰሙ ጊዜ እጅግ ተደስተው እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ ከዚህም በኋላ አቡነ ብስጣውሮስን እንደ ሕጋቸውና እንደ ሥርዓታቸው የሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም አበምኔትና ዓቃቤ ሰዓት በማድረግ ሾሟቸው፡፡
አቡነ ብስጣውሮስም በአቡነ ኢየሱስ ሞዐ ወንበር በተቀመጡ ጊዜ የተሰወረውን ሁሉ የሚያዩ ሆኑ፡፡ ፊታቸውም እንደ ጨረቃ የሚያበራበት ጊዜ ነበር፣ ለአገልግሎትም ወደ ቤተ መቅደስ በገባ ጊዜ ቅዱሳን መላእክት ክንፋቸውን እየጋረዱ ይቀበሉት ነበር፡፡ ጻድቁ ጸሎተ ዕጣን ሲያሳርጉ እያለቅሱ ነበር፤ የጌታችንን መከራ እያሰቡ ሰውነታቸውን በድብቅ ይገርፋሉ፤ ድኆችንና ጦም አዳሪዎችን ሁሉ የሚንከባከቧቸው አባት ሆኗቸው፡፡ ገዳሙንም አፍርሰው ሊዘርፉ የመጡትን ወራሪዎች አባታችን ወደ መቅደስ እየገቡ በጸሎት እያሰሯቸው አሳፍረው ይመልሷቸው ነበር፡፡ አቡነ ብስጣውሮስ በእንዲህ ዓይነት ተጋድሎ ገዳሙንና ሀገራችንን እየጠበቁ ሲኖሩ በመሀል የቅብዐት እምነት ነገር በገዳሙ ተነሣ፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችንን አምላካችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ‹‹ከትስብእት ጋር ከተዋሐደ በኋላ መንፈስ ቅዱስ ተቀባ፣ በዚህም ቅብዐት በጸጋ ልጅ፣ ንጉሥም፣ ነቢይም፣ ሊቀ ካህናትም ተባለ›› የሚሉ ከሃዲያን ተነሡና የእግዚአብሔር ሰው ብፁዕ አባታችን ብስጣውሮስ ይህንን የክሕደት ትምህርት ሰምተው እጅግ እያዘኑና እያለቀሱ የካዱትን ሰዎች በብዙ ምሳሌ እያደረጉ ማስተማር ጀመሩ፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመንፈስ ቅዱስ ቅብዐት በጸጋ ልጅ እንዳልሆነ፣ ነገር ግን በባሕርይው የአብ ልጅ እንደሆነ፣ እርሱ ራሱ ቅብ፣ እርሱም ራሱ ቀቢ፣ እርሱ ራሱ ተቀቢ እንደሆነ በብዙ ምሳሌ እያደረጉ የቀደሙ የአባቶቻችንንም ትምህርት ሁሉ እየጠቀሱ አስተማሯቸው፡፡ ነገር ግን ሰይጣን አንድጊዜ አስክዷቸዋልና አንዳንዶቹ እምቢ አሏቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ሐዋርያት ከመሠረቷት አንዲት ቤተ ክርስቲያን አውግዘው ለዩአቸው፤ ቤተ ክርስቲያንም ሰላም ሆነች፡፡ በዚህም አባታችን ከሃድያንን የሚዘልፉ ዳግማዊ ቄርሎስ ተባሉ፡፡ ይህም ክህደት መጀመሪያ ሰይጣን ለጳውሎስ ሳምሳጢን ያስተማረው ነው፡፡ ጳውሎስ ሳምሳጢን በገዳም ቅጠል እየበላ የሚኖር ተሐራሚ መናኝ ነበር፡፡ በጾም በጸሎት ሲኖር ሰይጣን ራሱን ሰውሮ መጥቶ ተገለጠለትና ‹‹ጸሎትህ በእግዚአብሔር ዘንድ ተሰምቶልሃል፤ ነገር ግን አምላክ ያለሩካቤ በድንግልና የተወለደ አይምሰልህ በሩካቤ ተወለደ እንጂ፤ ይህም ልጅ ደግ ሰው ሆነ፣ በ30 ዘመኑ በዮሐንስ እጅ በዮርዳኖስ ተጠመቀ፣ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል በራ ላይ ተቀመጠ፣ ያን ጊዜም ይህ ሰው በጸጋ የሥላሴ ልጅ ሆነ›› ብሎ አስተማረው፡፡ ጳውሎስ ሳምሰጢንም ሰይጣን የነገረውን ነገር በልቡ አምኖ ለደቀ መዝሙሩ ለተያስሮስ አስተማረው፡፡ ተያስሮስም ለድያድርስ አስተማረው፡፡ ድያድርስም ለንስጥሮስ አስተማረው፡፡ ንስጥሮስም ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችንን አምላካችንን ‹‹መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ዕሩቅ ብእሲ ነው›› ብሎ ለልዮንና ለመርቅያን አስተማራቸው፡፡
ንስጥሮስ ይህን አዲስ የክህደት ትምህርት እንዳመጣ በሰሙ ጊዜ 200 ኤጲስ ቆጶሳት በቅዱስ ቄርሎስ ዘእስክንድርያ መሪነት በኤፌሶን ተሰብስበው ሲያስተማሩት እምቢ ቢላቸው አውግዘው ለዩት፡፡ ንስጥሮስም ሰውነቱ መግሎ ክፉ አሟሟት ሞተ፡፡ በኋላም መርቅያን ሲነገሠና ልዩንም የሮም ሊቀ ጳጳስ ሲሆን ሁለቱም አባታቸው ንስጥሮስ ያስተማራቸውን ሃይማኖት ማስፋፋት ቻሉ፡፡ እነ ልዮንም ንስጥሮስ በተወገዘበት ጉባዔ ላይ የነበሩትና አሁን ለሥጋቸው የፈሩ አባቶችን ይዘው ከንስጥሮስ ክህደትና ከቅዱስ ቄርሎስ ትምህርት አወጣጥተው የራሳቸውን የረከሰ ሃይማኖታዊ ድንጋጌ አወጡ፡፡ ‹‹ክርስቶስ ሁለት አካል ነው፣ አንዱ የማርያም ልጅ አንዱ የእግዚአብሔር ልጅ በመቀራረብ አንድ ሆኑ ያለውን አውጥተው ከቅዱስ ቄርሎስም ቃልና ከንስጥሮስ ክህደት ቀላቅለው መለኮት የመለኮትን ሥራ ይሠራል፣ ትስብእትም የትስብእትን ሥራ ይሠራል፤ በሁለት መንገድ አንዱ ተአምራትን ያደርጋል ሁለተኛው መከራን ይቀበላል ስለዚህም ትስብእት ከመለኮት ያንሳል›› ብለው ጻፉ፡፡ ይህንንም የክህደት ጽሕፈታቸውን ለቅዱስ ዲዮስቆሮስ ላኩለት፡፡ እርሱም ሄዶ ከክህደታቸው እንዲመለሱ አስተማራቸው፡፡ ‹‹በአንዱ ክርስቶስ ላይ ለምን የሁለትነት ነገር ትናገራላች? ወደ ሠርግ ቤት ተጠርቶ የሄደው ውኃውንም የወይን ጠጅ ያደረገው እርሱ አንዱ ክርስቶስ ነው…›› እያለ በብዙ ምሳሌ ካስተማራቸው በኋላ ልዮንንና መርቅያን የጻፉትን የክህደት ጽሕፈት በፊታቸው ቀደደው፡፡ እነርሱ ግን አንድ ጊዜ ክደዋልና የቅዱስ ዲዮስቆሮስን ፂሙን ነጭተው ጥርሱን አውልቀው ብዙ አሠቃዩት፡፡ እርሱም የነጩትን ፂሙንና ያወለቁትን ጥርሱን ሰብስቦ ‹‹እነሆ የሃይማኖቴን ፍሬ ተቀበሉ›› ብሎ ለእስክንድርያ ክርስቲያኖች ላከላቸው፡፡ ከሃዲያኑም ወደ ጋግራ ደሴት አጋዙትና በዚያው ዐረፈ፡፡
ሰይጣን ለመጀመሪያ ጊዜ ለጳውሎስ ሳምሳጢን ያስተማራትን ያችን ክህደት በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ሰይጣን የሚያድርባቸው ሰዎች እየተቀባበሏት እስከ ንስጥሮስንና እስከ ልዮን ድረስ ከደረሰች በኋላ የልዮን ልጅ በሆነው በአውፍንስ አማካኝነት በዐፄ ሱስንዮስ ዘመን ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሀገራችን ኢትዮጵያ ገባች፡፡ አውፍንስም ክህደቱን ለሁለት የሀገራችንን መነኮሳት አስተማራቸው፡፡ ለአንደኛው ‹‹ወልድ ሦስት ልደት አለው፣ በመጀመሪያ ከአብ ተወለደ ዳግመኛም በመንፈስ ቅዱስ ሥጋ ከድንግል ተወለደ ሦስተኛም በቤቴልሔም ተወለደ›› ብሎ ካስተማረውና ካስካደው በኋላ ስሙን ‹‹ተክለ ሃይማኖት›› ብሎ ጠራው፡፡ ሁለተኛውንም መነኩሴ ለብቻው ጠርቶት ‹‹ልጄ ሆይ ስማኝ ልብ አድገህም ዕወቅ፣ ወልድ በመንፈስ ቅዱስ ቅብዐት የከበረ ነው፣ ይኸውም ሳይዋሃድ ማደር ነው›› ብሎ ካስተማረውና ካስካደው በኋላ ስሙን ‹‹ኤዎስጣቴዎስ›› ብሎ ጠራው፡፡ እነዚህም የካዱ ሁለቱ መነኮሳት በየሀገሩና በየአውራጃው እየዞሩ ሀገራችን ኢትዮጵያን በክህደት ትምህርታቸው አጥፍተዋት ነበር፤ ነገር ግን ብዙ ቅዱሳን አባቶቻችንና እናቶቻችን ይህን ክህደት በትምህርታቸውና በተአምራታቸው እንዲገታ አድርገውታል፡፡ አቡነ ብስጣውሮስም እነዚያን ከሃዲዎች አውግዘው ለዩአቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ከሃዲያኑ አባታችንን ከሰሷቸውና ከጎንደሩ ንጉሥ ጋር አጣሏቸው፡፡ ንጉሡም የእነዚያን ካሃዲዎች እምነት አምኖ ተቀብሎ ነበርና አባታችንን ወደ ጎንደር እንዲያመጧቸው ጭፍሮቹን ላከ፡፡ አቡነ ብስጣውሮስም ነገሩን አውቀው ስለ ቀናች ሃይማኖት ይመሰክሩ ዘንድ አንደበት እንዲሆናቸው ጌታችንን በጸሎት ሲጠይቁ ጌታችንም ‹‹ልጄ ብስጣውሮስ ሆይ አይዞህ እኔ ከአንተ ጋር ነኝ፣ እኔ ስለመሠረትኳት አንዲት ሃይማኖት ጽና›› አላቸው፡፡ አባታችንም ወደ ንጉሡ ዘንድ ሄዱና ንጉሡ ሰዎቹን ስለማውገዙ ጠየቃቸው፡፡ አባታችንም ንጉሡን ስለ ቀናች ሃይማኖት እየመሰከሩለት አስተማሩት፡፡ ንጉሡም በብዙ ስጦታና ሽንገላ ሊያታልላቸው ሞከረ ነገር ግን አባታችን አጥብቀው ተቃወሙት፡፡ ንጉሡም ዕውቀታቸውንና ጽናታቸውን ባየ ጊዜ አባታችንን በእግር ብረት አሳስሮ አሥር ቤት ውስጥ ጣላቸው፡፡ በዚህም ጊዜ የእግር ብረቱ እንደሰም ቀልጠ፡፡ ወታደሮቹም ይህንን ተአምር አይተው ፈርተው ሄደው ለንጉሡ ነገሩት፡፡ ንጉሡም ሰምቶ ደነገጠ፤ እየፈራና እየተንቀጠቀጠ ወደ አባታችን መጥቶ ሰገደና ‹‹አባቴ ሆይ ይቅር በሉኝ የሃይማኖትንም ነገር እንደገና አስተምሩኝ›› አላቸው፡፡ እሳቸውም አስተምረው ባረኩት፡፡ በመከራቸውም ታግሰው ለልጆቻቸውና ለእኛም የሐዋርያትን ሃይማኖት አጸኑልን፡፡ ዕድሜአቸውም 90 ዓመት በሆነው ጊዜ ዕረፍታቸው እንደደረሰ ዐውቀው የቀናች ሃይማኖት በሀገራችን ለዘለዓለም ጸንታ ትኖር ዘንድ ጌታችንን አጥብቀው ለመኑት፡፡ ጌታችንም በደሙ የመሠረታት የቀናች ሃይማኖት በሀገራችን ጸንታ እንደምትኖርና ሌላም የምሕረት ቃልኪዳን ከገባላቸው በኋላ ግንቦት 19 ዐረፉ፡፡
በዚያችም ዕለት ሐይቅ አለቀሰች፤ የሐይቅም ባሕር ሦስት ዓመት በኃይል ስትታወክ አቡነ አላኒቆስ ይህ ሁሉ የሆነው ስለ አባታችን ስለ ብስጣውሮስ ማረፍ መሆኑን ዐውቀው ወደ ንጉሡ ሄደው የአባታችንን ዐፅም እንዲሰጣቸው ጠየቁት፡፡ ንጉሡ ግን ‹‹በረድኤታቸው ይጠብቁኛልና አልሰጥም›› አላቸው፡፡ ንጉሡ ስለከለከላቸው አቡነ አላኒቆስም ቁስቋም ወደምትባል በወርቅና በከበረ ዕንቁ ወደተሸለመች ወደ እመቤታችን ቤተ ክርስቲያን ሄደው በእመቤታችን ሥዕል ሥር ወድቀው አለቀሱ፡፡ ሥዕሏም በሰው አንደበት አናግራ ካጽናናቻቸው በኋላ የአባታችን ዐፅም ከመሠዊያው በስተቀኝ በኩል እንደሚገኝ ነገረቻቸው፡፡ አቡነ አላኒቆስም ዐፅማቸውን አፍልሰው ወደ ሐይቅ በተመለሱ ጊዜ የመዓዛው ሽታ የንጉሡን አገር ሁሉ መላው፤ መቃብሩ በነበረበት ቦታም የብርሃን ዓምድ ተተክሎ ታየ፡፡ ንጉሡም መነኩሴው የአባታችንን ዐፅም እንደወሰዱ ባወቀ ጊዜ መነኩሴውን ይዘው ከአባታችን ዐፅም ጋር ያመጡለት ዘንድ ብዙ ፈረሰኛ ወታደሮቹን ላካቸው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር በጥበቡ ሰውሯቸዋልና አቡነ አላኒቆስን ሊያገኟቸው አልቻሉም፡፡ አቡነ አላኒቆስም የቅዱስ አባታችንን ዐፅም ወስደው በሐይቅ በመሠዊያው በስተቀኝ በኩል በቀበሩት ጊዜ በፊት ያስቸግር የነበረው የበሐሩ ኃይለኛ ንውጽውጽታ በአንድ ጊዜ ጸጥ አለ፡፡ ሌላም ብዙ ተአምራት ተደርገው ታዩ፡፡ ይኸውም ፍልሰተ ዐፅማቸው የካቲት 8 ቀን የተፈጸመ ነው፡፡
የአራቱ ቅዱሳን ነገሥታት፡- ከላስታ (ከዛጉዌ) ነገሥታት መካከል ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ፣ ቅዱስ ገብረ ማርያም፣ ቅዱስ ላሊበላና ቅዱስ ነአኵቶለአብ እነዚህ አራቱ ነገሥታት እንደ መልከጼዴቅ (ዘፍ 14፡18) ክህነትን ከንግሥና፣ ቅድስናን ከንጽሕና ጋር አንድ አድርገው በመያዝ እግዚአብሔርንም ሰውንም በቅድስና አገልግለው አልፈዋል፡፡ በንግሥናቸው ሀገርን በመልካም ሥራና በቅድስና ከማስተዳደራቸው በተጨማሪ ቅዱሳን ጻድቃን ሆነው እግዚአብሔርን በብዙ ድካም በመልካም ተጋድሎአቸው ያገለገሉና አገልግሎታቸውም ሆነ ቅድስናቸው በእግዚአብሔር ዘንድ ስለተመሰከረላቸው ጌታችን የሰጣቸውን ቃልኪዳን መሠረት በማድረግ ቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን የቅድስና ማዕረግ ሰጥታ፣ በስማቸው ቤተክርስቲያን አንጻ፣ ጽላት ቀርፃ በዓላቸውን እያከበረች መታሰቢያቸው ተጠብቆ ለዘለዓለም እንዲኖር አድርጋለች፡፡
ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ፡- ግንቦት 19 ቀን ሲወለድ እንደነ ተክለሃይማኖትና እንደነ ዜና ማርቆስ ወደ ምሥራቅ ዞሮ አምላኩን ያመሰገነ ሲሆን ቤቱም በብርሃን ተሞልቶ ታይቶ አዋላጆቹን ሁሉ አስገርሟል፡፡ እርሱ ገና ሳይወለድ በፊት አጎቱ ጠንጠውድም በንግሥና ላይ ሳለ ‹‹ከአንተ በኋላ የሚነግሠው ይምርሃነ ክርስቶስ የሚባል ሰው ነው›› ተብሎ ሲነገረው ‹‹እንዲህ የሚባል ሰው በቤተ መንግሥቴ አለን?›› በማለት ቢጠይቅም እንደነቢዩ ኤርሚያስ ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ የተመረጠ ሕፃን እንደሚወለድ ነግረውታል፡፡ አርባ ዓመት የነገሠው ጠንጠውድም ቀድሞ በትንቢት እንደተነገረው ‹‹ይምርሃነ ክርስቶስ›› የሚባል የወንድሙ ልጅ መወለዱን ሲሰማ ‹‹የወንድሜን ልጅ አየው ዘንድ አምጡልኝ›› ብሎ ላከ፡፡ ባየውም ጊዜ ደም ግባቱ እጅግ ያምር ስለነበር ‹‹ይህስ መንግሥቴን ይውረስ፣ በእውነት ልጄ ነው›› ብሎ ባረከው፡፡ ሆኖም ከእርሱ ጋር ስምንት ቀን ተቀምጦ በወለዳቸው ልጆቹ መካከል በተመለከተው ጊዜ በልቡ ሰይጣን አደረበትና በቅናት ሆኖ ‹‹እርሱ ነግሦ ልጆቼ ወታደሮቹ ሊሆኑ ነው›› በማለት ይገድለው ዘንድ አሰበ፡፡ ሆኖም ግን ‹‹ለጊዜው ምንም አያውቅም ለወደፊቱም የንግሥና ምሥጢር እንዳያውቅ ወደ እናቱና አባቱ ዘንድ መልሰው በዚያ ከብት ሲያግድ ያድጋል እንጂ ሥርዓተ ንግሥናን አያውቅም›› በማለት ስለተመከረ ወደ እናቱ ላከው፡፡ በኋላም በጥበብና በብልሃት አስተዋይ ሆኖ ማደጉን በሰማ ጊዜ ሊገድለው አሽከሮቹን ላከ፡፡ እናቱም ተላኩት አሽከሮች ምግብ አቅርባ እርሷ ግን ነገሩን እንዲገልጽላት እግዚአብሔርን በስውር አልቅሳ ስትለምን የንጉሡ ተንኮል ስለተገለጠላት ልጇን ደበቀችው፡፡ በስውርም ወስዳ ከጳጳሱ ዘንድ ዲቁና እንዲቀበል ካደረገችው በኋላ ‹‹ልጄ ሆይ! አጎትህ ሊገድልህ ይፈልግሃልና በፊቴ ከሚገድልህ ርቀህ ብትሄድ ይሻላል፣ ያዕቆብን ከኤሳው የጠበቀ አንተንም ይጠብቅህ›› ብላ ሸኘችው፡፡ ንጉሡ አጎቱም ‹‹ይምርሃነ ክርስቶስን ፈልጎ ላገኘልኝ የመንግሥቴን እኩሌታ እሰጣለሁ›› ብሎ ቢያውጅም ይምርሃነ ክርስቶስ ግን ወደ ኢየሩሳሌም ተሰደደ፡፡ በዚያም የሌዋውያን ወገን የምትሆን ቅድስት ሕዝባን አግብቶ ቅስናም ተቀብሎ ሥጋዊውንና መንፈሳዊውን ጥበብ ተምሮ ካጠናቀቀ በኋላ ወንጌልን እየሰበከ፣ በተአምራቱም ሕመምተኞችን እየፈወሰ እግዚአብሔር እያገለገለ ኖረ፡፡ እግዚአብሔርም አጎቱ ንጉሥ መሞቱንና በንጉሡም ዙፋን እርሱ እንደሚነግሥ ነግሮት በመልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል መሪነት ወደ ኢትዮጵያ ተመልሶ መጥቶ በላስታ ወረዳ ሳይ (ዛሬ ሸጐላ ማርያም) ከምትባል ሀገር ደርሶ በዚያ ወንጌልን እያስተማረ፣ ድውያንን እየፈወሰ ተቀመጠ፡፡ ትምህርቱንና ተአምራቱን ያዩት የአካባቢው ሰዎች ‹‹ነፃነትና ፍቅር የሚገኝብህ የእግዚአብሔር ሰው ሆይ! እኛ ሰላማዊ ብርሃናዊ ብለን ስም አወጣንልህ፣ ያንተ ግን ስምህ ማን ይባላል ንገረን›› አሉት፡፡ እርሱም ‹‹ስሜ ይምርሃነ ክርስቶስ ነው›› ባላቸው ሰዓት ሕዝቡ ሁሉ በሹክሹክታ ‹‹ይምርሃነ ክርስቶስ የሚባል ሲነግሥ ሃይማኖት ይቀናል፣ ፍርድ ይስተካከላል፣ በዘመኑም የሮም ሰዎች ለኢትዮጵያ ይገዛሉ›› ሲሉ አባቶቻችን ሰምተናል አሉ፡፡ ከጠንጠውድምም ሞት በኋላ ማንም እንዳልነገሠ ሲያረጋግጡ የማን ልጅ እንደሆነ እንዲነግራቸው በእግዚአብሔር ስም ለመኑትና ‹‹የጠንጠውድም የታናሽ ወንድምና የዣን ስዩም ታላቅ ወንድም የሆነው የግርማ ስዩም ልጅ ነኝ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹የተነገረው ትንቢት ደርሷልና ሳንዘገይ እናንግሠው›› ብለው ሥርዓተ መንግሥቱን ፈጽመው በዙፋን ላይ አስቀመጡት፡፡
ለቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ መስቀል ከሰማይ እንደወረደለት፡- ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ በትረ መንግሥቱንም ከያዘ በኋላ ሁሉም ሰው እንደወንጌሉ ቃል በአንድ ለአንድ ጋብቻ ብቻ ተወስኖ እንዲኖር በግዛቱ ሁሉ አወጀ፡፡ እግዚአብሔርም የሚመሰገንበት ቤት መሥራት አሰበና የተፈቀደለትን ቦታ እንኪያገኝ ድረስ ዛዚያ በምትባል ልዩ በሆነች ስፍራ ድንኳን ተክሎ እንደሙሴ እግዚአብሔርን ማገልገል ጀመረ፡፡ ዘጸ 33፡7፡፡ ሰኔ 21 ቀንም ቀድሶ ሕዝቡን ከማቁረቡ በፊት ኅብስቱንና ጽዋውን የእግዚአብሔር መልአክ ሕዝቡን ከሚባርክበት ሰማያዊ መስቀል ጋር ከሰማይ አምጥቶለታል፡፡ በዚህ ዓይነት ሁኔታ ሕዝቡን ከሰማይ በወረደለት መስቀል እየባረከና ሰማያዊውን ኅብስትና ጽዋ እያቆረበ ለ22 ዓመት በድንኳኗ ውስጥ ኖሯል፡፡ ዛሬም ድረስ ያንን ሰማያዊው መስቀል በቤተመቅደሱ የሚያገለግሉት ካህናት አባቶች ቤተመቅደሱን ለመሳለም የሚመጣውን ሕዝበ ክርስቲያን በበዓል ቀን ይባርኩበታል፡፡
መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለይምርሃነ ክርስቶስ ተገልጦለት ቤተመቅደሱን ሥራ ብሎ እንደነገረውና ቃልኪዳን እንደሰጠው፡- ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ሰማያዊ ኅብስትና ጽዋ እየወረደለት ለ22 ዓመት በድንኳኗ ውስጥ ካገለገለ በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በክብር ተገልጦለት እንዲህ አለው፡- ‹‹ወዳጄ ይምርሃነ ክርስቶስ ይህን ሥፍራ (ዛዚያን) ልቀቅ፣ ከእንግዲህ ወዲህ በዚህ ቦታ ሰማያዊ ኅብስትና ሰማያዊ ጽዋ አይወርድልህም፡፡ ወደማሳይህ ቦታ ተነሥተህ ሂድ፣ በዚያም እስከ ዕረፍትህ ቀን ድረስ ሰማያዊ ኅብስትና ሰማያዊ ጽዋ ይወርድልሀል፡፡ ይህን ዓለም ለማሳለፍ እስከምመጣበት እስከ ዕለተ ምፅዓት ድረስ የእኔ ጌትነት የአንተም የቅድስና ሕይወት የሚነገርበት፣ የሥጋህ የዕረፍት ቦታ የሚሆንበት፣ ለምትሠራው መቅደስ ክዳን የሚሆን ሣር የማይፈልግ ሰፊ ዋሻ አለ፣ በዚያ ቤተ መቅደሴን ሥራ፣ እኔም በምትሠራው ቤተ መቅደስ ከአንተ ጋር ለዘለዓለም ቃልኪዳኔን አቆማለሁ፡፡ በምታንጸው ቤተ መቅደስ ውስጥ ‹አቤቱ የይምርሃነ ክርስቶስ አምላክ ሆይ! ስለወዳጅህ ስለ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ብለህ ይቅር በለኝ› እያለ ‹አባታችን ሆይ!› የሚለውን ጸሎት የሚጸልይ ዕለቱን እንደተጠመቀ አደርገዋለሁ፡፡ ወደ አንተ በእምነት ከኃጢአቴ እነፃለሁ ብሎ በእምነት የሚመጣውን ሁሉ ከእናትቱ ማኅፀን እንደተወለደ ሕፃን ልጅ አድርገዋለሁ፤ ኃጢአቱንም ይቅር እለዋለሁ፣ ኃጢአቱ ከባድ ጭነት እንደያዘች መርከብ ቢከብድም እንደገለባ አቀልለታለሁ፣ እንደቀይ ግምጃ ቢሆንም እንደነጭ ፀምር (ግምጃ) እንደጥቁር በርኖስ ቢሆንም እንደበረዶ አነፃዋለሁ፤ በስምህ የለመነኝን ሁሉ እሰጠዋሁ፣ ወደ መቃብርህም ቦታ እኔና የባሕርይ አባቴ አብ የባሕርይ ሕይወቴ መንፈስ ቅዱስ በፍቅር ካልሳብነውና በረድኤት ካላቀረብነው በቀር ሊመጣ የሚችል የለም፡፡ በመቃብርህ እየዞረ ‹የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ አምላክ ሆይ! ስለወዳጅህ ስለ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ብለህ ይቅር በለኝ፣ ይምርሃነ ክርስቶስ ሆይ በቃልኪዳንህ ጠብቀኝ (ይምርሃ ፍታኝ)› እያለ የሚጸልየውን አንተ በከበርክበት ክብር አከብረዋለሁ፡፡ የእኔን ጌትነት፣ የአንተን የቅድስና ሕይወት የሚንቅ የሚያቃልል ግን ንስሐ ካልገባ በቀር ከሰማያዊ ክብር የተለየ ይሆናል፡፡ የዕረፍትህን መታሰቢያ የሚያደርግ፣ በአማላጅነትህ ለሚታመን፣ ገድልህን የሚጽፍና የሚያጽፍ የዘላለም ክብርን አጐናጽፈዋለሁ፤ ገድልህን የሚያነብ በአንዷ ቃል ሰባት እጥፍ ክብር በመንግሥተ ሰማያት እሰጠዋለሁ፤ ወደዚህች ቦታ አንተን ብሎ የመጣውን እንግዳ ሁሉ ካላሰበበት ቦታ አላሳድርብህም፤ በምታንጸው ቤተ መቅደስ በዕረፍትህ መታሰቢያ ቀን ከጠዋት እስከ ማታ ተግቶ የሚጸልይ በስሜ ከሞቱ ከ144,440 የቤቴልሔም ሕፃናት ጋር እቆጥረዋለሁ፤ ለቤተ መቅደስህ ዕጣን ያገባ ሥጋዬ እንደተገነዘበት እንደ ኒቆዲሞስ ሽቱ እቀበለዋለሁ፣ አልባሳት የሚያገባ ኒቆዲሞስና ዮሴፍ ሥጋዬን እንገነዙበት መግነዝ አደርግለታለሁ፤ ለመሥዋዕት የሚሆን ንጹሕ የግብር ስንዴ፣ ወይን (ዘቢብ) የሚያመጣውን እንደ መልከጼዴቅ እቀበለዋለሁ፤ ለመብራት የሚሆን ጧፍ፣ ሰም ሌላም የቤተ መቅደስ መገልገያዎችን ሁሉ ለቤተ መቅደስህ የሚያገባ በሰማያዊ ክብር አከብረዋለሁ፡፡ ነገ ማለዳ ተነሥተህ ወግረ ስሂን ወደሚባለው የዕረፍትህ ቦታ ወደሚሆነው ዋሻ ሕዝብህን አስከትለህ ሂድ፤ በዚያም ቤተ መቅደሴን ሥራ›› ብሎ ጌታችን ቃልኪዳን ከሰጠው በኋላ ሰላምታ ሰጥቶት በክብር ወደ ሰማይ ዐርገ፡፡ ቤተመቅደሱንም አንጾ ሲጨርስና በዕረፍቱም ቀን በድጋሚ ተገልጦለት ይህንን ቃልኪዳን ደግሞለታል፡፡
ይምርሃነ ክርስቶስ ቤተ መቅደሱን የሚሠራበትን ቦታ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል እንዳሳየው፡- ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ከመድኃኔዓለም ክርስቶስ ቃልኪዳን ከተቀበለ በኋላ አገልጋዮቹን አስከትሎ ሲጓዝ ቀድሞ ግፃት ትባል ከነበረችው ዛሬ ግን ወግረ ስሂን ከምትባለው ሰፊ ዋሻ ሲደርስ ቅዱስ ሩፋኤል ‹‹እግዚአብሔር ያዘዘህ ቦታ ይህ ነው፣ በዚህ ቤተ መቅደሱን ሥራ›› አለው፡፡ ዙሪያው በደን የተሸፈነ ስለነበር የዋሻውን መግቢያ እያስቆረጠ ሲሄድ የአካባቢው ሰዎች ደም እያፈሰሱ ለአጋንንት መሥዋዕት የሚያቀርቡበት አንድ ወይራ ነበርና አገልጋዩ ክርስቶስብነ ያንን ዛፍ ሲቆርጠው በውስጡ ያደረው ሰይጣን ክርስቶስብነን አንቆ ጣለው፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ሩፋኤል አዛፍ ከሚባል ሀገር ወስዶ ጣለው፡፡ የቅድስት ኢየሉጣ ልጅ ሰማዕቱ ቅዱስ ቂርቆስም በአፀደ ነፍስ ብፁዕ ይምርሃነ ክርስቶስን ረድቶታል፡፡ ይህም ታሪክ በገድለ ቅዱስ ቂርቆስ 3ኛ ተአምር ላይ በሰፊው ተጠቅሷል፡፡ ይህንንም ቀጥሎ ባለው ርዕስ ላይ እናየዋለን፡-
በቅዱስ ቂርቆስ ገድል ላይ ሕፃኑ ቂርቆስ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስን እንደረዳው ተጽፏል፡- ‹‹በቅድስት ሀገር በሮሐ ከአምላኩ ዘንድ የክህነትን ሥልጣን የተቀበለ የዓለምን ተድላ ደስታ ንቆ መንግሥቱን ከተወ በኋላ በገዳም ሲኖር ለ40 ዓመት ያህል በበዓላትና በየሰንበቱ ከሰማይ ኅብስትና ወይን የወረደለት አንድ ጻድቅና ካህን ነበር፡፡ የጽድቁም ምልክት እስካሁን ክቡር ሥጋው ካረፈበት ሥፍራ አለ፡፡በመንግሥቱ ሳለ በእግዚአብሔር ፈቃድ መንፈስ ቅዱስ ባመለከተው ቦታ በባሕር ላይ ቤተ ክርስቲያን ሊያንጽ ተነሣ፡፡ ንጉሥ ይምርሃነ ክርስቶስን የቤተ ክርስቲያኑን መሠረት ለማሳመር ሁሉ እያንዳንዱ ደንጊያና ሸክላ አንጨትም እንዲሸከም ትእዛዙን ይነግር ዘንድ በግዛቱ ዓዋጅ ነጋሪ አዞረ፡፡ ንጉሡም ከባሕር ዳርቻ ቆሞ አገልጋዩ በባሕሩ ላይ ለቤተክርስቲያኑ መሠረት ርብራብ ሊያደርግ ከባሕሩ ገባ፡፡ ይህንንም ሲያደርግ የባሕር ጋኔን ወጥቶ መታው፣ ፈጥኖም ሞተ፡፡ ንጉሥ ይምርሃነ ክርስቶስ የሰይጣንን መተነኳኮል አይቶ አብዝቶ አዘነ፡፡ በዚህ ጋኔን ስለሞተ አገልጋዩ ስለ ቤተክርስቲያንም መታነጽ የሚያደርገውን ሲያስብ ስለጽድቅ የተጋደለ ማር ቂርቆስ ድንገት በታላቅ ክብር ተገልጦ ‹የተቀባህ ንጉሥ የከበርህም ካህን ሆይ! በአምላኬ ሥልጣን የሞተ አገልጋይህን እኔ አስነሣልሃለሁ፣ ጋኔኑንም እበቀለዋለሁ፣ አንተም ኃይል በተደረገልህ ሥፍራ በምትሠራት መቅደስ ውሰጥ በስሜ የተሠየመ ታቦት ታኖራለህ› አለው፡፡ ንጉሡም ‹የክርስቶስ ሰማዕት ሆይ! እንዳልኸው አደርጋለሁ› ብለ መለሰ፡፡ ያንጊዜም ማር ቂርቆስ እጁን ዘርግቶ የጋኔኑን የራስ ጠጉር ይዞ ከባሕር ውስጥ አወጣው፡፡ ቁመቱ ፈጽሞ ረጅም፣ ሁለንተናውም በእሳት እንዳቃጠሉት የእንጨት ግንድ ጥቁር ነበር፡፡ ከቅድስት ሀገር ከሮሐ ወደ ጎጃም ምዕራባዊ ክፍል እንደ ድንጊያ ወረወረው፣ በዚያም ሞተ፤ የሞተው የንጉሡ አገልጋይ ግን ከሞት ተነሣ፡፡ ንጉሡም ፈጽሞ ደስ ተሰኘ፡፡ አምስት ጊዜ ከሩቅ የዞጴ እንጨት እየተሸከመ ያችን መቅደስ ሠራት፡፡ ከአገልጋየቹም ጋር ሲሠራ ይውል ነበር፡፡ ጌታ ኢየሱስም የመቅደስ ሥራዋን እያመለከተው ከእርሱ ጋር ነበረ፡፡ የመቅደስ መታነጽም ከተፈጸመ በኋላ ንጉሥ ይምርሃነ ክርስቶስ በከበረ ሕፃን ቂርቆስ ስም የተሠየመ ታቦት በውስጧ አኖረ፡፡ ኅብራቸው ባማረ የከበሩ ጌጦችና ልብሶችም አስጌጣት፡፡ በውስጧም በጥቅምት 19 ቀን ቀደሰ፡፡›› (ገድለ ቅዱስ ቂርቆስ ወኢየሉጣ ገጽ 98-100)
ወደ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ገድል እንመለስና ጻዲቁ ንጉሥ ጌታችን እንዳዘዘው ቤተመቅደሱን ሊሠራ መንገዱን አስመንጥሮ ወደ ዋሻው ሲደርስ ትልቅ ባሕር አገኘ፡፡ ‹‹በዚህ ላይ እንዴት ቤተመቅደስ ልሠራ እችላለሁ?›› ብሎ ሲጨነቅ ከሰማይ ‹‹በባሕሩ ላይ እንጨት፣ በእንጨቱ ላይ ሣር፣ በሣሩ ላይ ጭቃ፣ በጭቃው ላይ ደረቅ አፈር አድርገህ ደልድለህ ቤተ መቅደሴን ሥራ›› የሚል ቃል መጣለት፡፡ ቀድሞውንም በነቢዩ ዳዊት ላይ አድሮ ‹‹ምድርን በውኃ ላይ ያጸና ምሕረቱ ለዘለዓለም ነውና›› (መዝ 135፡6) እንደተባለ አሁን ደግሞ በዚህ ጻዲቅ ንጉሥ እጅ ቤቱን በባሕር ላይ እንዲሠራ ፈቀደ፡፡ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስም በታዘዘው መሠረት መሥሪያዎቹን ሲሰበስብ የቅድስና ሕይወቱን የሰሙ የግብፅና የሮም ሰዎች ለመስኮት የሚሆኑ የከበሩ ድንጋዮችን (ዕምነ በረዶችን) አመጡለት፡፡ ውድ የሆኑና የከበሩ ዓለቶችንና እንጨቶችን አምጥቶ በኪነጥበባዊ ቅርጻ ቅርጾችና በሥነ ሥዕል እጅግ ውብ አድርጎ በተፈጥሮአዊ አቀማመጡ ፍጹም አስደናቂ የሆነውን ቤተመቅደሱን ሠርቶ እንደጨረሰ ሲራዳው የነበረውን የቅዱስ ቂርቆስን ታቦት አስገብቶ ከሰማይ በወረደለት መስቀሉ ሕዝቡን እየባረከ፣ ሰማያዊ ኅብስትና ሰማያዊ ጽዋ እየወረደለት እግዚአብሔርንና ሰውን ሲያገለግል ኖረ፡፡ ቅዱስ ሩፋኤልም በዘመኑ ሁሉ ይራዳው ነበር፡፡
ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ያሳነጸውን ቤተመቅደስ እንደገና በወርቅና በብር አክብሮ ለማነጽ ወደ እግዚአብሔር በጸሎት ቢጠይቅ ጌታችን ተገልጦለት ‹‹ቤተ መቅደስህ የታጸበትን የከበረ ድንጋይ ከወርቅና ከብር ከዕንቁም ይልቅ አከበርኩልህ፣ በወርቅና በብር ያነጸከው እንደሆነ የኋላ ሰዎች ወርቅና ብሩን ሲሉ ቤተክርስቲያንህን ያፈርሱብሃል›› ብሎታል፡፡ ቤተመቅደሱ የተሠራው በባሕር ላይ ለመሆኑ ማሳያ ይሆን ዘንድ ከቤተ መቅደሱ ሰሜናዊ ጫፍ በኩል ወደ ታች ወደ ምድር ውስጥ የምትከፈት ትንሽ መስኮት አለች፣ እርሷ ስትከፈት ውኃው ከሥር ይታያል፡፡ ይህን ግን ማሳየት የሚችሉት አባቶች ብቻ ናቸው፡፡ በዋሻው በቤተልሔሙ በኩል ውስጥ ለውስጥ እስከ አቡነ ዮሴፍ ተራራ ድረስ የሚወስድ ፍጻሜው ያልተገኘ መንገድ አለ፡፡ የቤተክርስቲያኑ አገልጋዮች በዋሸው ውስጥ ለውስጥ የ4፡30 መንገድ ያህል በመብራት ከተጓዙ በኋላ የያዙት መብራት ስላለቀባቸውና ፍርሃትም ስለያዛቸው የመንገዱን ፍጻሜ ሳያገኑት ተመልሰዋል፡፡
ቁጥራቸው ከ5ሺህ በላይ የሆኑ የሮምና የግብፅ ጳጳሳት የይምርሃነ ክርስቶስን በረከት ሊቀበሉ እንደመጡ፡- ከዚህ በኋላ የእግዚአብሔርን ጌትነትና የይምርሃነ ክርስቶስ የቅድስና ሕይወት በዓለም ሁሉ መሰማት ጀመረና የሮም ሰዎችም ወደ እርሱ መጥተው 55 ውድ መስቀሎችን በስጦታ ገበሩለት፡፡ እግዚአብሔር በእርሱ ላይ የሚያደርገውን ተአምርና ቅድስናውን የሰሙ ቁጥራቸው 5740 የሆኑ የግብፅና የሮም ጳጳሳትና ኤጲስቆጶሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት እንዲሁ መነኮሳት ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ የሚወርድለትን ሰማያዊ ኅብስትና ሰማያዊ ጽዋ በእጁ ለመቀበልና በመስቀሉ ለመባረክ መጡ፡፡ የግብፁ ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ አትናቴዎስም ‹‹ከዚህ ቅዱስ የእግዚአብሔር አገልጋይ እጅ በረከትን መቀበል እሻለሁ›› ብሎ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ከቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ጋር ተገናኝቶ ሁለቱም በረከትን አንዳቸው ከአንዳቸው ተቀብለዋል፡፡ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስም ወደ እርሱ ለመጡት 5740 ደጋግ ጳጳሳትና ኤጲስቆጶሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት እንዲሁ መነኮሳት ሁሉ ቀድሶ ሰማያዊውን ሥጋ ወደሙን አቀብሏቸዋል፡፡ እነርሱም ሰማያዊውን ሥጋና ሰማያዊውን ደሙን ከተቀበሉ በኋላ ‹‹ይህን ባየንበትና በቀመስንበት ሌላ አናይም አንቀምስም ብለው የተወሰኑት ወደሌላ የሀገራችን ገዳማት የሔዱ ሲሆን ብዙዎቹ ደግሞ ከእርሱው ጋር አብረው በዚያው ዐርፈው ተቀብረዋል፡፡ ዛሬም ድረስ የእነዚህ ቅዱሳን አፅም ቤተ መቅደሱ ካለበት ጀርባ በኩል በሚገኘው ትልቅ ዋሻ ውስጥ በክብር ተቀምጦ ይገኛል፡፡
የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ መካነ መቃብር፡- ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስን ዕረፍቱ እንደደረሰ ነግሮት ታላቅ ቃልኪዳን ከሰጠው በኋላ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ጥቅምት 19 በታላቅ ክብር ዐርፏል፡፡ የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ መካነ መቃብር የሚገኘው ራሱ ባሳነጸው መቅደስ በስተ ደቡብ አቅጣጫ ሲሆን በግምጃ የተሸፈ ነው፡፡ ለጻዲቁ ንጉሥ በተሰጠው ቃልኪዳን መሠረት አማኞች መእመናን መቃብሩን እየዞሩ ‹‹የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ አምላክ ሆይ! ስለወዳጅህ ስለ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ብለህ ይቅር በለኝ፣ ይምርሃነ ክርስቶስ ሆይ በቃልኪዳንህ ጠብቀኝ (ይምርሃ ፍታኝ)›› እያሉ በመዞርና አባታችን ሆይ የሚለውን ጸሎት እየጸለዩ ከቃልኪዳኑ በረከት ይሳተፋሉ፡፡
የአቡነ ዓቢየ እግዚእን ገድል ደግሞ አንዴ ለራሴ ልዝለቀው እመለስበታለሁ፡፡ ደሞ እየጻፍኩት ሳለ መብራት ጠፋ....እይይ...ምቀኛ!
መብራት ሄዶ ቆይቶ አሁን ስለመጣ የአቡነ ዓቢየ እግዚእን ገድል አሁን አካትቼዋለሁ፡፡
አቡነ ዓቢየ እግዚእ፡- አባታቸው ያፍቅረነ እግዚእ እናታቸው ጽርሐ ቅዱሳን ይባላሉ፡፡ ሁለቱም ሃይማኖታቸው የቀና ምግባራቸው ያማረ በእግዚአብሔር የተወዱ ናቸው፡፡ በወርቅ በብር የከበሩ ቢሆኑም ልጅ ግን አልነበራቸውም፡፡ በእመቤታችን ስም ለተቸገሩ ምጽዋትን በመስጠት ዘወትር ይማጸኑ ነበር፡፡
አንድ ቀን ድንቅ የሆነ ራእይ አየና ፈቃደ እግዚአብሔርን ሲጠባበቁ ነሐሴ 7 ቀን ጽርሐ ቅዱሳን ፀነሰችና ግንቦት አንድ ቀን እንደ ፀሐይ የሚያበራ ልጅ ወለደችና በ40 ቀኑ ሲጠመቅ ስሙን ዓቢየ እግዚእ አሉት፡፡ ያጠመቁትም የአክሱሙ ሊቀ ጳጳስ መተርጉም ሰላማ ሲሆኑ እሳቸውን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ሕጻኑን እንዲያጠምቁት በማዘዝ በክንፎቹ ተሸክሞ ከአክሱም ወደ ተንቤትን ምድረ መረታ አመጣቸውና አጠመቁት፡፡ እርሳቸውም ‹‹ይህ ሕጻን ድውይ የሚፈውስ ሙታንን የሚያነሣ ቅዱስ ይሆናል›› ብለው ትንቢት ተናግረዋል፡፡ ያፍቅረነ እግዚእ እና ጽርሐ ቅዱሳን እንግዳን መቀበል ልማዳቸው ነበርና አንድ ቀን ሦስት አጋንንት በሽማግሌ አምሳል ሆነው በእንግድነት እቤታቸው ገቡና ‹‹ልጃችሁን የሐዋርያትን መጻሕፍትን መዝሙረ ዳዊትንና አርጋኖንን እንድናስተምርላችሁ ስጡን›› አሏቸው፡፡ ወላጆቹም ገና ሕጻን መሆኑን በመናገር ሲከራከሩ ቅዱስ ሚካኤል ደርሶ እነዚያን አጋንንት አጠፋቸው፡፡ አጋንንቱም ይህንን ዘዴ ተጠቅመው ሕጻኑን ዓቢየ እግዚእ ወስደው ሊገድሉት ነበር ምክንያቱም በእርሱ ምክንያት ነፍሳት እንደሚድኑ ዐውቀዋልና፡፡
ገና ከልጅነታቸው ጀምሮ የእግዚአብሔርን ከጠሩበት ምንም ነገር ከማድረግ ወደኋላ አይልም ነበር፡፡ ከልጆችም ጋር ሲጫወቱ ልጆቹ ‹‹ስለ እግዚአብሔር ብለህ ይህን አድርግልን…›› ሲሉት ያደርግላቸዋል፡፡ በእረኝነት ሳሉ ምሳውንም ሆነ እራቱን ለምስኪኖች ይሰጣል፡፡ ለእግዚአብሔር ስም እጅግ ቀናተኛ ስለነበሩ ስሙን ይፈሩ ስለነበር ስመ እግዚአብሔርን ጠርተው ‹‹ይህን ክፉ ነገር በራስህ ላይ አድርግ›› ባሏቸው ሰዓት እንኳን በራሳቸው ላይ አንዳች ክፉ ነገር ወይም አደጋ ለማድረስ ወደኋላ አይሉም ነበር፡፡ ይህንን ሊፈትኗቸው ብለው አንድ ቀን ስለታማ ጦር አምጥተው ‹‹ስለ እግዚአብሔር ብለህ እስቲ ራስህን በዚህ ስለታማ ጦር ትወጋ ዘንድ ና›› ባሏቸው ጊዜ አብርሃም ልጁን ይስሃቅን ሊሠዋ በኅሊናው እንደወሰነ እርሳቸውም በቁርጥ ኅሊና ሆነው ራሳቸውን በጦሩ ሊወጉ ሲሉ ዘለው ያዟቸው፡፡ በሌላም ጊዜ እንዲሁ ሊፈትኑት በጭነት ምክንያት ጀርባው የቆሰለ አህያ አምጥተው ‹‹ዓቢየ እግዚእ ስለ እግዚአብሔር ብለህ የዚያችን አህያ ቁስሏን ላስ›› አሉት፡፡ እርሱም ያን ጊዜ ‹‹ርኩስን ብስም ኃጢአት ይሆንብኛል፣ አይሆንም ካልኳቸው ደግሞ ስመ እግዚአብሔርን ጠርተንበት እምቢ አለ ስለሚሉ የፈጣሪዬን ስም መዳፈር ይሆንብኛል ብሎ በልቡ አሰበና ያን ጊዜ ይስም ዘንድ ተመለሰ፡፡ ባልንጀሮቹም በቁርጥ ኅሊናው እንደወሰነ ባወቁ ጊዜ ሊያደርገውም ሲሄድ ተመልከተው ቶሎ ብለው ሮጠው ከኋላው ያዙት፡፡ እርሱም ‹‹እኔስ የፈጣሪዬን ስም እፈራለሁ ስሙን ተደፋፍሬ በምድር በሕይወት ከምኖር ሞት ይሻለኛል›› አላቸው፡፡
ከዚህም በኋላ ወላጆቹ ለመምህር ዘርዐ ሚካኤል ሰጡትና ብሉያት ሐዲሳት መጻሕፍትን ሌሎችንም አስተማረው፡፡ ከዚህም በኋላ መምህሩንና ዓቢየ እግዚእን ቅዱስ ሚካኤል ነጥቆ ወስዶ አክሱም አደረሳቸውና ዓቢየ እግዚእ ከአባ ሰላማ መተርጉም እጅ ዲቁናና ቅስና ተቀበሉ፡፡ ከብዙ ዘመንም በኋላ የሃሌ ሉያው አባ ሳሙኤል ቆብንና አስኬማን ሰጠው፡፡ ለአባታችን አንበሶችና ነብሮች አራዊትም ሁሉ እንደ ጓደኛ ሆነው ታዘዙለት፡፡ ቶራዎችም በሰው አንደበት ያናግሩታል፡፡ ቶራዎቹም ከነብሮች ጋር ተስማምተው እንዲኖሩ ያደርጋቸዋል፡፡ እርሱም እህልን ሳይቀምስ በቤት ጣሪያም ውስጥ ገብቶ ሳይቀመጥ ተጋድሎውን በማብዛት ብዙ ደከመ፡፡ የመላእክት ክንፍ ተሰጥቶት በሦስት ሰዓት ውስጥ የሕያዋንን መኖሪያ አይቶ ይመለሳል፡፡ በዋልድባ ገዳም ስውር ቤተ ክርስቲያን አለ ነገር ግን የሚያገኘው አልነበረም፡፡ አባታችን ዓቢየ እግዚእ ግን 40 ቀንና 40 ሌሊት ከጾመ ከጸለየ በኋላ አራዊት ተሸክመውትና አጅበውት እዚያች ስውር ቤተ ክርስቲያን ዘንድ ደረሰ፡፡ በውስጧም የሚንቀሳቀስ ብርሃን አየ ይኸውም የዚህ ዓለም ብርሃን አይደለም፡፡ በውስጧ ያሉ ስውራን ቅዱሳንንም አገኛቸውና ከእነርሱ ተባረከ፡፡ ከዚህም በኋላ የተለያዩ አስደናቂ ተአምራትን እየሠራ ወንጌልን በመስበክ ብዙ አገለገለ፡፡ የተከዜን ባሕር ለሁለት ከፍሎ በመሻገር በአካባቢው ያሉ ኢስላሞችን በተአምራቱ አሳመናቸው፡፡ ከደረቅ ጭንጫም ላይ ውኃን አፈለቀ፡፡ በተሰሰጠውም ክንፍ ብሔረ ሕያዋንና የጌታችን መካነ መቃብር ዘንድ እየሄደ ከቅዱሳን ጋር ጸሎት ያደርጋል፡፡ ደቀ መዛሙርቶቹም ‹‹እገሌ ሞቷልና የት እንቅበረው? ባሉት ጊዜ እርሱ ግን ከጸለየ በኋላ ከሞት ያስነሣዋል፡፡ የሐማሴኑ መስፍንም እንዲሁ በጦርነት ወቅት ሞቶ ባለሟሎቹ አስክሬኑን ተሸክመው ወደ ሀገሩ ሲወስዱት ሰላምጌ ከምትባል የላስታ ምድር ደረሱና በመንገድ አባታችንን አገኛቸውና ‹‹ይህን በድን ወዴት ትወስዱታላችሁ?›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹ሐማሴን ይባላል በንጉሡ ትእዛዝ ወደ ጦርነት ዘምተን ሳለ እርሱ ሞቶ ወደ ሀገሩ እየወሰድነው ነው›› አሉት፡፡ አባታችንም ያስቀምጡት ዘንድ አዘዛቸውና ውኃ አምጡልኝ አላቸው፡፡ ስመ እግዚአብሔርንም ጠርቶ ከጸለየና በውኃው ካጠመቀው በኋላ ሐማሴንን ከሞት አስነሣው፡፡ ሐማሴንንም ስለ አሟሟቱ ሲጠይቁት ‹‹መልአከ ሞት ወስዶ ለፍርድ ሳያቆመው በፊት ይህ ጻዲቅ መነኩሴ ስለ እኔ ሲለምን አየሁት፤ በጸሎቱም እግዚአብሔር ማረኝና ነፍሴን ወደ ሥጋዬ እንድትገባ አዘዘ›› ብሎ የሆነውን ሁሉ በዝርዝር ነገራቸው፡፡ አባታችንም ሐማሴንን ‹‹በሰላም ወደ ሀገርህ ሂድ›› ብሎ አሰናበተው፡፡ ያ ሹም ግን ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች መጽውቶ ወደ አባታቸን ዘንድ መጣ፡፡ የአባታችንን ጽድቁንና ትሩፋቱን የሰሙ ሁለት ሺህ ሰዎችም አብረውት ከሹሙ ጋር መጡና አባታችንን ‹የምንኩስና ልብስ ልንለብስ እንወዳለን›› ባሉት ከፈተናቸው በኋላ አመነኮሳቸው፡፡ ያንንም መስፍን ፍኖተ ሕይወት-የሕይወት መንገድ ብሎ ሰየመው፡፡ የአባታችንም ያችን ደብር ሰጠውና አበ ምኔት ሆኖ ብዙ አገልግሎ ዘመኑን ጨረሰ፡፡ ዳግመኛም አባታችንን በደብረ መድኃኒት በምትባል ደብር ሳለ ስሟ ቡሩክት ማርያም የምትባል ልጁ ሞታ አባታችን አለቀሰላት፡፡ ተነሥቶም ወደ ዋሻ ገብቶ በሩን ዘግቶ አመድ ነስንሶ ደረቱን እየደቃ እየጸለየ ሳለ ቡሩክት ማርያም ከሞት መነሣቷን ደቀ መዛሙርቱ ሮጠው መጥተው ነገሩትና ሄዶ አገኛት፡፡ ‹‹ምን አየሽ?›› ቢላት እርሷም ‹‹‹ስለአገልጋዬ ዓቢየ እግዚእ ልቅሶና መቃተት ይህች ነፍስ ወደ ሥጋዋ ትመለስና እስከምታረጅ ትኑር› የሚል ቃል ሰማሁ›› አለችው፡፡ እርሷም አባታችን ካረፉ በኋላ በምድረ ዠመዶ ኖራ በኋላ በሰላም ዐረፈች፡፡ ከዕለታትም በአንደኛው ቀን ብፁዕ አባታችን ከ6 መነኮሳት ልጆቻቸው ጋር ይሰግዱ ዘንድ ሲሄዱ ርዝመቱ 120 ስፋቱ 12 ክንድ የሆነ ዐይኖቹ እንደሚነድ እሳት የሆኑ ከአፉም ነበልባል የሚወጣ እንደንስርም ክንፍ ያለው ከዚህ በፊት ታይቶ የማይታወቅ መጠኑም ተራራ የሚያክል አውሬ በቁጣ ሊውጣቸው አፉን ከፈተ ምላሱን አውለበለበ፡፡ መነኮሳቱም እጅግ ደንግጠው ሳለ አባታችን ግን በስመ ሥላሴ አማትበው በአውሬው ላይ የተገለጠውን ያንን ከይሲ ለሁለት ሰነጠቁት፡፡ አንዲት እናት ወደ አባታችን መጥታ ‹‹የአንተን የጸሎት ውኃ ስጠኝ?›› አለችው፡፡ አባታችንም ‹‹ምን ልታደርጊው ነው?›› ሲላት ‹‹ልጠጣው ነው›› አለችው፡፡ እርሱም ስመ እግዚአብሔርን ጠርቶ ‹‹…አቤቱ ይህንን የጸሎት ውኃ ለሚጠጣው ሁሉ የሚያድን አድገው…›› ብሎ ጸልዮ በስመ ሥላሴ አማትቦ ሰጣት፡፡ እርሷም ወደቤቷ ወስዳ ሌላኛዋን ሴት ‹‹ይህንን የጸሎት ውኃ እጠመቅ ዘንድ በላየ ላይ አፍሽልኝ›› አለቻት፡፡ ሁለተኛዋም ሴት በላይዋ ልታፈስ ውኃውን አነሣች፣ ከፍም አደረገችው፡፡ ነገር ግን ውኃው የረጋ ደም ሆነ፣ አልፈሰሰምም፡፡ እነዚያም መበለታት እጅግ ደንግጠው ‹‹በኃጢአታችን ውኃው ደም ሆነ፣ ወደ አባታችን ሄደን አንንገረው›› ተባብለው ሄደው ነገሩት፡፡ አባታችንም ‹‹ያደረጋችሁት ምንድነው?›› ሲላቸው ሴቷ ‹‹በራሴ ላይ አፍስሽልኝ ከማለቴ በስተቀር ምንም ያደረግነው የለም›› አለችው፡፡ አባታችንም ‹‹ቃልን ከመለወጥ በላይ ሌላ ኃጢአት ምን የለም፣ ቃልሽን ስለለወጥሽ ደም ሆነ፣ እኔን ‹የምጠጣው የጸሎት ውኃ ስጠኝ› አልሽኝ እኔም እንዳልሽኝ ሰጠሁሽ›› አላት፡፡ እርሱም ‹‹አምጭው›› አላትና ሰጠችው፡፡ ተቀብሎ በስመ ሥላሴ ሦስት ጊዜ ቢባርከው ያንጊዜ እንደቀደሞው ንጹሕ ውኃ ሆነ፡፡ ያችንም መበለት ‹‹ልትጠጪ ከወደድሽ ውሰጂ›› አላት፡፡ እነዚያም መበለታት ከምድር ላይ ወድቀው ‹‹ይቅር በለን›› ሲሉት እርሱም እጁን አንሥቶ ባረካቸው፡፡ አባታችን አንድ ቀን ደብረ ሊባኖስ ገዳም ገብቶ ሳለ ገዳማውያኑ ‹‹አንድ መነኮስ ብናገኝ ሥጋወደሙ በተቀበልን…›› ሲባባሉ አገኛቸውና ባረካቸውና ‹‹ዛሬ የተዘጋጀ ቁርባን አለን?›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹አዎን›› አባሉት ጊዜ አዘጋጂተው እንዲያመጡ አዘዛቸው፡፡ አዘጋጅተው አመጡና አባታችንን ‹‹ገብተህ ቀድስ›› አሉት፡፡ እሱም ‹‹ባርኩኝ›› አላቸውና ‹‹እንደ መልከጼዴቅ፣ እንደ አቤል መሥዋዕትህን ይቀበልልህ…›› ባሉት ጊዜ ሚመጠን አለ፡፡ ይህንንም ባለ ጊዜ ኅብስትና ጽዋ ከፃሕል ጋር ተዘጋጅቶ ከላይ ከሰማይ ወረደ፡፡ ይህንንም ያዩና ከእርሱ ጋር የነበሩ ሁሉ ‹‹ይህ ኅብስትና ጽዋ ከየት መጣ›› እያሉ አደነቁ፡፡ አባታችንም የሐዋርያትን ቅዳሴ ቀድሶ አቆረባቸው፡፡ አባታችንም ወጣና ደመናውን ጠቅሶ በደመና ተጫነ፡፡ እነርሱም ‹‹አቤቱ ስለ እግዚአብሔር ብለህ ስምህን ንገረን›› አሉት፡፡ እርሱም ‹‹ስሜ ዓቢየ እግዚእ ይባላል የምንኩስና ስሜ የመረታ ሀገር እንጦንስ ነኝ›› አላቸውና ባረኳቸው ሄደ፡፡ ያም ፃሕልና ጽዋ ዛሬም ድረስ አለ፡፡ ቅዱስ አባታችን በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ የተለያዩ አስደናቂ ተአምራትን እየሠራ ወንጌልን በመስበክ እገዚአብሔርን ካገለገለ በኋላ ከፈጣሪው ታላቅ ቃልኪዳን ተቀብሎ በዛሬዋ ዕለት በክብር ዐርፏል፡፡
የቅዱሳኑ ምልጃቸውና በረከታቸው በአማላጅነታቸው በምንታመን በሁላችን ላይ ይደርብን! አሜን!!!

የእግዚአብሔር መንግሥት መውረሻ ብቸኛ መንገድ በሆነችው በመጀመሪያዋ ንጽሕት ቅድስት በሆነችው በአባቶቻችን ሃይማኖት ያጽናን በእውነት!!! ተዋሕዶ ብቸኛና ፍጽምት ነሽ!