Sunday, November 27, 2016

በራእይ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እንደሚገኝ የታየው ታቦት ተገኘ

ቅ/ሚካኤል ሚዛንና ሰይፍ ይዞ በዩኒቨርሲቲው ፩ኛ በር በኩል እየወሰደ ያሳየኛል፡፡”
/ታቦቱ መኖሩን የጠቆሙት ባለራእዩ ባሕታዊ በለጠ ዘነበ/
*                    *                    *
aau-st-michael-ark
 
(አዲስ አድማስ፤ ዓለማየሁ አንበሴ፤ ቅጽ ፲፮ ቁጥር ፭፻፹፤ ቅዳሜ፣ ኅዳር ፲፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም.)
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 6 ኪሎ ካምፓስ ሙዝየም ውስጥ፣ ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ ያስቆጠረ ታቦት የተገኘ ሲኾን፤ ታቦቱ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንደተመለሰ ታውቋል፡፡
በዩኒቨርሲቲው ግቢ ታቦት ስለመኖሩ፣ “ራእይ ታይቶኛል” የሚሉ ባሕታዊ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ባስታወቁት መሠረት፣ ጥናት ተደርጎ መኖሩ በመረጋገጡ፤ ከዩኒቨርሲቲው ጋር ብዙ ድርድር ከተደረገ በኋላ፣ ኅዳር 10 ቀን 2009 ዓ.ም.፣ ታቦቱ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት መመለሱን በጉዳዩ ተሳታፊ የነበሩት መጋቤ ምሥጢር ቡሩክ አሣመረአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
“ታቦቱ በዐፄ ኃይለ ሥላሴ ጥያቄ እንደተቀረፀና የቅዱስ ሚካኤል ታቦት መኾኑን የሚገልጽ ማስታወሻ ተገኝቷል፡፡ ታቦቱ ከ68 ዓመት በላይ ዕድሜ እንዳለውም ታውቋል፤” ብለዋል – መጋቤ ምሥጢር ቡሩክ፡፡
ታቦቱ በዩኒቨርሲቲው ስለመኖሩ፣ ባሕታዊ በለጠ ዘነበ የተባሉ በራእይ ታይቶኛል በሚል በተደጋጋሚ ሲናገሩ እንደነበር የጠቆሙት መጋቤ ምሥጢር ቡሩክ፤ “ቅዱስ ሚካኤል ሚዛንና ሰይፍ ይዞ በዩኒቨርሲቲው ካምፓስ አንደኛ በር በኩል እየወሰደ ያሳየኛል፤” እያሉ ይናገሩ እንደነበርና፣ ይህንንም በ2003 ዓ.ም. አካባቢ ለፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ መግለጻቸውን፤ ነገር ግን ትኩረት የሚሰጣቸው ሳያገኙ መቅረታቸውን ያስታውሳሉ፡፡

ባሕታዊው፣ በ2007 ዓ.ም. ይህንኑ ራእይ ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ማሳወቃቸውንና የሚመለከታቸው የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሥራ ሓላፊዎች ጉዳዩ እንዲጠና ማዘዛቸውን መጋቤ ምሥጢር ቡሩክ አውስተው፣ በጥናቱም ጽላቱ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ መኖሩ መረጋገጡን ገልጸዋል፡፡ ይህን ተከትሎም ታቦቱ ለቤተ ክርስቲያንዋ እንዲመለስ ከዩኒቨርስቲው ጋር በርካታ የደብዳቤ ልውወጦች ተደርገዋል፡፡
መጀመሪያ ላይ ዩኒቨርሲቲው የጥናትና ምርምር ተቋም እንደመኾኑ፣ ቅርሶችን ተከባክቦ የመያዝና ለትውልድ የማስተላለፍ ሓላፊነት እንዳለበት በመግለጽ፣ ታቦቱን ለቤተ ክርስቲያንዋ ለመመለስ በእጅጉ ተቸግሮ ነበር፤ ይላሉ መጋቤ ምሥጢር ቡሩክ፡፡ ኾኖም ጽላት ለቱሪስቶች(ለጉብኝት) ክፍት ኾኖ መታየት የሌለበት የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያና  መግለጫ በመኾኑ፣ በዩኒቨርሲቲው ሙዝየም ውስጥ ቢቀመጥ ትርጉም እንደሌለው ስምምነት ላይ በመደረሱ፣ የመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን በአደራ ተረክቦ እንዲያስቀምጥ መደረጉን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ታቦቱ፣ አልተረስቶን በሚል ስያሜ፣ በመዝገብ ቁጥር 1761 ተመዝግቦ የተገኘ ሲኾን፣ ሚስተር ስቴፈን ራይት በተባለ ሰው፣ እ.አ.አ ሰኔ 12 ቀን 1961 ወደ ሙዝየም መግባቱን መጋቤ ምሥጢር ይናገራሉ፡፡ ነገሥታት ታቦት አስቀርፀው በቤተ መንግሥታቸው በሚገኙ አብያተ ጸሎታት(ሥዕል ቤቶች) የማስቀመጥ ልምድ እንደነበራቸው የጠቀሱት መጋቤ ምሥጢር ቡሩክ፤ ምናልባትም ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ይህን የቅዱስ ሚካኤል ታቦት ሳያስቀርፁት እንዳልቀረ ግምት መኖሩን አመልክተዋል፡፡ “ታቦቱ በዩኒቨርሲቲው ሙዝየም 3ኛ ምድር ቤት ውስጥ ለብቻው በተሠራ ቤት ውስጥ ተደብቆ ነው የተገኘው፤ የሙዝየሙ ሠራተኞች እንኳን ታቦት መኖሩን አያውቁም ነበር፤” ብለዋል መጋቤ ምሥጢሩ፡፡
ከሰኔ 12 ቀን ጀምሮ፣ ከመልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ጋር ይገናኙ እንደነበር የገለጹት ባለራእዩ ባሕታዊ በለጠ ዘነበ፣ በተደጋጋሚ ወደ ፓትርያርኩ ጽ/ቤት እየሔዱ ቢናገሩም ትኩረት አለማግኘታቸውን ጠቅሰው፣ በኋላ የቤተ ክርስቲያኒቱ የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽንና የቤተ መዛግብትና ቅርስ ክፍል ሓላፊዎች ባደረጉት ከፍተኛ ጥረት ታቦቱን ከዩኒቨርስቲው ለመረከብ መቻሉን ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የታሪክ ምሁር የኾኑትን ፕ/ር አሕመድ ዘካርያን ስለ ጉዳዩ ጠይቀናቸው ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ ሳይኾኑ ቀርተዋል – “አኹን ብዙም የምገልጸው ነገር የለም፤” በማለት፡፡
the-imperial-genete-leul-palace-and-menbere-leul-st-mark-church
የቀድሞው ገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት(የአኹኑ የአ.አ.ዩ. የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም – በግራ) 
እና የመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን(በቀኝ)
በዩኒቨርሲቲው ሙዝየም የተገኘውን የቅዱስ ሚካኤል ታቦት አስመልክቶ፣ ለብዙኃን መገናኛ እና ለሕዝብ ይፋ ለማድረግ፣ ለጥር 8 ቀን 2009 ዓ.ም. መርሐ ግብር መያዙን መጋቤ ምሥጢር ቡሩክ አስታውቀዋል፡፡
አኹን በ6 ኪሎ የሚገኘው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ፣ የግርማዊ ቀዳማዊ ንጉሠ ነገሥት ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት የነበረ ሲኾን፣ ታቦቱን በአደራ የተረከበው የመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያንም፣ የንጉሠ ነገሥቱና ቤተሰቦቻቸው ሥዕል ቤት(ጸሎት ቤት) ኾኖ ያገለገለ ነው፡፡ የ1953 ዓ.ም. መፈንቅለ መንግሥት ተከትሎ የንጉሡ ቤተ መንግሥት ወደ ኢዮቤልዩ በመዛወሩ፣ የገነተ ልዑል ቤተ መንግሥትን ለትምህርት ተቋምነት በስጦታ አበርክተዋል፤ ጸሎት ቤት የነበረው የመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያንም ለሕዝብ አገልግሎት የሚሰጥ ኾኗል፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ: ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ ያስቆጠረ ታቦተ ቅዱስ ሚካኤል ተገኘ

የቅዱስ ገብርኤል ጽላት በአንድ አባት ራእይ ተገኘ

Tuesday, November 15, 2016

የእመቤታችን የቤት እቃዎች በግብጽ

እመቤታችን በግብፅ ውስጥ በነበረችበት ወቅት ልጅዋን ኢየሱስ ክርስቶስን ሦስት አመት ከስድስት ወር ከ10 ቀን ሲሆን  እመቤታችን በወቅቱ ትገለገልበት የነበረው ሙቀጫዋ ፣ድስቷ እንዲሁም: ጌታችንን ገላዉን ልብሱን ታጣጥብበት የነበረዉ ከዲንጋይ የተሰራ መገልገያ ዕቃዎችዋ ሲሆን ይህን ቅዱስ ስፍራ ለማየት የታደሉት ምዕመናን ጭምር ደስታቸውን በእልልታ ና በዝማሬ በድምቀት እያከበሩት ይገኛል።