Showing posts with label የተሰወሩ የደብረ ዓሣው አባ ዮሐኒ. Show all posts
Showing posts with label የተሰወሩ የደብረ ዓሣው አባ ዮሐኒ. Show all posts

Wednesday, December 9, 2015

የደብረ ዓሣው አባ ዮሐኒ

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
ኅዳር 5- የደብረ ዓሣው አባ ዮሐኒ የተሰወሩበት ዕለት ነው፡፡ አባታቸው አባ አሞኒም በዚህች ዕለት ነው ያረፉት፡፡ ዳግመኛም ዛሬ የቅዱስ ሌንጊኖስ ራስ የታየችበትና ተአምር ያረገችበት ዕለት ነው፡፡ 

የቅዱስ ለንጊኖስ ራስ የታየችበት ተአምር ያረገችበት ዕለት፡- ይኸውም ቅዱስ ለንጊኖስ በመጀመሪያ ጌታችንን ጎኑን በጦር የወጋው ነው፡፡ የመድኃኔዓለም የፍቅሩ መጠን ልክ የለውምና ይህንንም ጎኑን በጦር የወጋውን ሰው በወቅቱ ዕውር የነበረችውን አንድ ዐይኑን አበራለት በኋላም በስሙ አምኖ ወንጌልን ሰብኮ በሰማዕትነት እንዲያርፍ መረጠው፡፡ በሙሉ ልቡ አምኖ እስከሞት ድረስ ለመታመን ተዘጋጅቶ በክፉዎች አይሁድ ፊት ስለ ጌታችን አምላክነት መመስከር ጀመረ፡፡ አይሁድና ሮማውያንም በምስክርነቱ እጅግ ተቆጥተው ያሳድዱት ጀመር፡፡ ወደ ታናሹዋ እስያ ወደ ቀጵዶቅያ ሄዶ በዚያ ወንጌልን እንደ ሐዋርያት በመስበክ ብዙዎችን ወደ ቀናች እምነት መልሷቸዋል፡፡ አይሁድም በክፋት ተነሥተው የሐሰት ምስክር አቁመው በመኳንንት ዘንድ በሐሰት ወንጅለው በቀጵዶቅያ አገር ሐምሌ 23 ቀን አንገቱን በሰይፍ አስቆረጡት፡፡ ራሱንም ብቻዋን ወደ ኢየሩሳሌም ወሰዷት፡፡ በምስክርነቱ የቀኑና የተናደዱ በዚያ የሚኖሩ አይሁድም ራሱ ተቆርጣ ባዩአት ጊዜ እጅግ ተደስተው ከከተማ ውጭ በአንድ ኮረብታ ላይ ቀበሯት፡፡
ከብዙ ቀንም በኋላ በቅዱስ ለንጊኖስ ስብከት ያመነች አንዲት ሴት በቀጵዶቅያ አገር ራሱን ከቆረጡበት ጊዜ ጀምራ በተቆረጠበት ቦታ በመቆም ስለእርሱ ታለቅስ ነበር፡፡ ከጊዜም በኋላ ዐይኖቿ ታወሩ፡፡ የጌታችንን መቃብር ለመሳለም ተነሥታ ከነልጇ ወደ ኢየሩሳልም መጣች፡፡ ኢየሩሳልም በደረሰችም ጊዜ ልጇ ሞተ፡፡ በሀዘንም ሆና ሳለ ወደ ሀገሯ መርቶ የሚወስዳት ስላጣች መሪር ልቅሶን አልቅሳ ደክሟት ተኛች፡፡ ተኝታም ሳለ ቅዱስ ለንጊኖስን ከሞተ ልጇ ጋር በራእይ አየችው፡፡ ራሱ ተቀብራ ያለችበትንም ቦታ ነገራትና ሄዳ እንድታወጣ አዘዛት፡፡ ቅዱስ ለንጊኖስ ወዳመለከታት ወደ ቦታው ሄዳ ስታስቆፍረው መዓዛው እጅግ ጣፋጭ የሆነ የሽቱ መዓዛ ወጣ፡፡ አማኟም ሴት የቅዱስ ለንጊኖስ ራሱ ያለችበት ቦታ ስትደርስ ታላቅ ብርሃን ተገለጠላትና ዐይኖቿ በሩላት፡፡ የቅዱስ ለንጊኖስን ራስና የልጇን ሥጋ ይዛ ወደ ሀገሯ ወስዳ ባማረ ቦታ አኖረቻት፡፡ ይኸም ተአምር ኅዳር 5 ቀን የተፈጸመ ነው፡፡
/////////////////////////
አቡነ አሞኒና ልጃቸው አቡነ ዮሐኒ፡- መጽሐፍ አባታቸውን ዘስዩመ ተንቤን እሁሁ ይላቸዋል፡፡ እናታቸው ደግሞ ዓመተ መንፈስ ቅዱስ የሚባሉ ደገኛ ምግብራቸው ያማሩ ሀገር ወዳድ ናቸው፡፡ አቡነ አሞኒ የካቲት 5 ቀን አክሱም ውስጥ ሲወለዱ ሰይጣናት የወላጆቻቸውን ቤት ከበው በማየታቸው እንደተወለዱ በእጃቸው ቢያመለክቱ በአንድ ጊዜ 60 ሰይጣናት ተሸንፈው እንደጢስ በነው ጠፍተዋል፡፡ አሞኒ ማለት አሸናፊ ማለት ነው፡፡

አባ አሞኒ የራስ ፀጉራቸው ልብስ መጎናጸፊያ ሆኖላቸው የኖሩ ታላቅና ቀደምት አባት ናቸው፡፡ በደመና ተጭነው ደብረ ዘይት ድረስ በመሄድ ከአባ እብሎይ ጋር ተገናኝተው ብዙ ምሥጢርን አውርተዋል፡፡ አባ ዮሐኒን ያሳደጉት አስተምረው ያሳደጓቸው አባ አሞኒ ናቸው፡፡ የእናቱን ጡት ፈጽሞ ጠብቶ የማያውቀውን የመንፈስ ቅዱስ ልጃቸውን አባ ዮሐኒን እሳቸው እያጫወቱት የታዘዘ አሞራ በክንፎቹ እያለበሰው ቶራ (ሰሳ) እያጠባችው ነው ያደገው፡፡ መነሻ ታሪኩም እንዲህ ነው፡-

የተንቤን አውራጃ ገዥ የነበረው ሰው በዘመኑ ዐፄ ካሌብ የነበሩበት ዘመን ነበርና አብሯቸው ወደ ምድረ ኖባ ሄደው ሰባት ዓመታትን የፈጀ የጦር ዘመቻ ክርስያኖችን በሚያሠቃዩ ነገሥታት ላይ አዳሄዱ፡፡ የተንቤኑ አውራጃ ገዥም ወደ ዘመቻው ከሄደ ቆይቶ ነበርና ታናሽ ወንድሙ የገዥውን ሚስት ‹‹ወንድሜ የቀረው ሞቶ ነው እንደ ኦሪቱ ሕግ እኔው ላግበሽና ልጆቹን ላሳድግ›› አላት፡፡ እርሷም ‹‹ባሌ ቢሞት ይነገረኝ ነበረዘመቻ የሄደው ሁሉ አልተመሰም›› ብላ እምቢ ብትለው በግድ ተገናኛት፡፡ በዚህም ጊዜ አባ ዮሐኒ ተፀነሱ፡፡ በሚያዝያ 5 ቀንም ተወለዱ፡፡
ከዘጠኝ ወር በኋላ ማሏ ከዘመቻ መጣና ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡ የአካባቢውም ሰው ወጥቶ በክብር ሲቀበለው ሚስቱ ግን ምጥ ተይዛ ታማ ስለነበር ወጥታ አልተቀበለችውም፡፡ ‹‹የት ሄደች? ምንስ ሆነች?›› ብሎ ሲጠይቅ ልጅ አይደብቅምና አንድ ሕፃን ‹‹አርግዛ ልትወልድ በምጥ ላይ ትገኛለች›› አለው፡፡ የአውራጃውም ገዥ ያለችበት ድረስ ሄዶ ቢያያት ያማረ ወንድ ልጅ ታቅፋ አገኛት፡፡ ከዚህም በኋላ ከቤቱ ምሰሶ ጋር ጥፍንግ አድርግ አስሮ እየገረፋትና እያስጨነቃት ከማን እንዳረገዘች ጠየቃት፡፡ እርሷም የወንድሙን ምሥጢር ለመጠበቅና ወንድማማቾቹን ላለማጣላት ሥቃዩን ታግሳ ዝም አለች፡፡ በዚህ ቅጽበት የራማው ልዑል ቅዱስ ገብርኤል 40 ዓመት ሙሉ ዘግተው በበረሃ ለሚኖሩት ለአባ አሞኒ ተገለጠላቸው እንደ አውሎ ነፋስ አምዘግዝጎ ወስዶ አውራጃ አገረ ገዥው ቤት አደረሳቸው፡፡
እንደደረሱ ዓመተ ማርያም በጽኑ ድብደባና ግርፋት እየተሠቃየች እያለ አባ አሞኒ የጸጉራቸውን አጽፍ ለብሰው ራቁታቸውን ደጇ ላይ ቆመው አየቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ለባሏ ‹‹ያውና ከዚህ መነኩሴ ነው የወለድኩት›› አለቸው፡፡ አተንቤቱ አውራጃ አገረ ገዥውም አባ አሞኒን ይዞ ጽኑውን ግርፋት በወታደሮቹ አስገረፋቸው፡፡ በመቀጠልም ገና የእናቱን ወተት እንኳን ያልቀመሰውን ጨቅላ ሕፃን አንሥቶ ‹‹እንካ ልጅህን ይዘህ ጥፋ ከዚህ›› ብሎ ሰጣቸው፡፡ አባ አሞኒም በዚህ ጊዜ ‹‹ዮ ሀበኒ ዮ ሀበኒ›› አሉ፡፡ በትግርኛ እሽ ስጠኝ ማለት ነው፡፡ ከዚህ በመነሳት ነው ሕፃኑ በኋላ ላይ ‹‹አባ ዮሐኒ›› የተባሉት፡፡ አባ አሞኒም ሕፃኑን ተረክበው ወደ ደብረ ዓሣ ተራራ ሥር ሄደው ልጁን ከወይራ ዛፍ ሥር አስተኝተው ‹‹አምላኬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ኃጢአቴን ተመራምረህ ይህንን ሕፃን የሰጠኸኝ አላጠባው ጡት የለኝ አላበላው እህል የለኝ›› ብለው የጨቅላው ሕፃን ነገር እጅግ ቢያስጨንቃቸው ምርር ብለው አለቀሱ፡፡ ጸሎታቸውንም እንደጨረሱ ተራራውን በመስቀል ምልክት ቢባርኩት በተራራው መሐል ላይ እንደመደብ ያለ አልጋ በተአምራት ተሠርቶ አገኙት፡፡ ሕፃኑንም ከዚያ አስተኝተው ድጋሚ ጸሎት ሲጀምሩ ቶራ (ሰሳ) መጥታ እግርና እግሯን አንፈራጣ ሕፃኑን አጠባችውና ሄደች፡፡
አባ አሞኒም በዚህ ደስ ተሰኝተው ሕፃኑን ‹‹የምግብህ ነገር ከተያዘ ግዴለም›› ብለው ሌሊቱን ሙሉ ሲጸልዩ አድረው መለስ ቢሉ ዳግመኛም ሕፃኑን የታዘዘ ንስር አሞራ በክንፎቹ ጋርዶ አልብሶትና አቅፎት እንዳደረ ተመለከቱ፡፡ አባታችንም እጅግ ደስ ተኝተው እግዚአብሔርን አመሰገኑት፡፡ እንደዚሁ ሁሉ ቀን ቀን ቶራዋ እያጠባችው ሌሊት ሌሊት ንስር አሞራው አልብሶት እያደረ ሕፃኑ ሦስት ዓመት ሆነው፡፡ አባ አሞኒም ከሰባት ዓመቱ ጀምረው እስከ 12 ዓመቱ ድረስ ፊደል፣ ንባብ ከነትርጓሜው፣ ብሉይንና ሐዲስን፣ ምግባር ሃይማኖትን ሥርዓተ ቤተ ክርስያንን ሁሉ አስተማሩት፡፡
አባ አሞኒ ልጃቸው አድጎ 12 ሲሆነው ከዚህም በኋላ ዲቁና ሊያሾሙትና አክሱም ጽዮን ወስደው ሊያስባርኩት ቤተ ካህናት ከተባለው ቦታ ይዘውት ሲሄዱ ልዩ ስሙ ሲሂታ ከሚባለው ቦታ ሲደርሱ ከወገባቸው በላይ እራታቸውን የሆኑ እንስራ የተሸከሙ ዓሥር ሴቶች አገኙ፡፡ አባ ዮሐኒም አባታቸውን ‹‹አባቴ እነዚህ ደረታቸው ላይ ቀንድ ያላቸው ጽጉራቸው የረዘመ ምንድናቸው? እንደእኛ የሆኑ መስህታን የሚባሉት እነዚህ ናቸውን?›› አሏቸው፡፡ አባ አሞኒም ‹‹አይደሉም ልጄ ዝም ብለህ ሂድ›› አሏቸው፡፡ በኋላ ግን ትዝ ሲላቸው ‹‹በዱር እንስሳት ያሳደኩት ልጄ ወንድና ሴት ለይቶ ሲያውቅ በዚያው ሊሳሳት አይደልምን?›› ብለው በማሰብ ዲቁናና ክህነቱ ይቅርበት ብለው ተመልሰው ወደ በዓታቸው ይዘውት ገቡ፡፡
ከዚህም በኋላ አባ አበይዶ ወደ አባ አሞኒ መጣና እሳቸውን ከአባ ዮሐኒ ጋር እያገለገሏቸው ተቀመጡ፡፡ ዮሐኒ እየጻፈ አበይዶ የሚጻፍበትን ቆዳ እያዘጋጁ ሦስቱም በአንድነት በተጋድሎ መቀመጥ ጀመሩ፡፡
አባ ዮሐኒ 20 ዓመት አባ አሞኒ ደግሞ 40 በሆናቸው ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለአባ አሞኒ ተገለጠላቸውና ‹‹አሞኒ ሆይ ከእንግዲህስ እግዚአብሔር ወደኔ ና ብሎሃል›› አላቸው፡፡ እሳቸውም ልጆቻቸውን አባ ዮሐኒንና አባ አበይዶን ጠርተው ‹‹በሉ እንግዲህ እኔ ወደ እግዚአብሔር መሄዴ ነውና ጸልዩልኝ›› አሏቸው፡፡ ከማረፋቸውም በፊት አባ ዮሐኒን ለብቻቸው ጠርተው ‹‹አንተ አባ ዮሐኒ ካሁን በፊት ሲሂታ ላይ ያየሃቸው ሴቶች ናቸው፣ አዳምንም ከገነት ያስወጡ ናቸው፡፡ ወደፊትም እንደ እነርሱ ያለ የደረሰብህ እንደሆነ ካለህበት ገደል ተወርውረህ ውደቅመ በባሕር ውስጥ ጥለቅ›› ብለው ነግረዋቸው በዛሬዋ ዕለት ኅዳር 5 ቀን በ160 ዓመታቸው በሰላም ዐረፉና ወደ ጠራቸው እግዚአብሔር ሄዱ፡፡
አባ አሞኒ ካረፉ ከ12 ዓመት በኋላ የአባ ዮሐኒ ወላጅ እናታቸው የልጇን ነገር ስታጠና ኖራ ነበርና አሁን ባሏም ስለሞተ አባ አሞኒም ስላረፉ ልጇን ልታይ ከ32 ዓመት በኋላ መጣች፡፡ ቀሚስ ለብሳ ፀጉሯን ተሠርታ በሴትነቷ ልጇ ካለበት ቦታ በመሄድ ማነጋገር እንደማትችል ስላወቀች ፀጉሯን ተላጭታ የወንድ ልብስ ቁምጣ ለብሳ በሁለመናዋ ወንድ መስላ ወደ ደብረ ዓሣ ተራራ አመራች፡፡ እዚያም እንደደረሰች በቅዱሳን ሥርዓት መሥረት ሦስት ጊዜ ‹‹አውሎ ግሶን፣ አውሎ ግሶን፣ አውሎ ግሶን›› አለች፡፡ ሰይጣን ይህን ስም ሲሰማ 40 ክንድ ይርቃል፡፡ የደብረ ዳሞ መነኮሳት እንደ ሰላምታ መለዋወጫ ይጠቀሙበታል፡፡ አባ ዮሐኒም ይህን ድምጽ ከውጭ በሰሙ ጊዜ ‹‹አንተ ማነህ?›› አሉ፡፡ እርሷም ‹‹ዓመተ መንፈስ ቅዱስ ነኝ›› አለቻቸው፡፡ አባታችንም አንድም ድምፁዋ ወትሮ ከሚያውቁት ድምፅ ስተለየባቸው ደግሞም ትዝ ሲላቸው እነዚያ እንስራ አዝለው ደረታቸው ላይ ቀንድ ያላቸው ሆነው ውኃ ቀድተው ሲሄዱ በመነገድ ያዩአቸው ሴቶች ድምፅ ሆነባቸው፡፡ ደግሞም ‹‹ወልደ እከሌ፣ ክንፈ እከሌ›› ሲባል እንጂ ‹‹ዓመተ፣ ወለተ›› ሲባል ሰምተው አያውቁም ነበርና አባታቸው አባ አሞኒ የነገሯቸው ትዝ አላቸው፡፡ በዚያውም ቅጽበት የሚጽፉባትን ብዕር ጆሮአቸው ላይ እንደሰኩ 500 ሜትር ርዝመት ካለው ትልቅ ተራራ ላይ ራሳቸውን ቁልቁል ወረወሩ፡፡ ነገር ግን መሬት ሳይደርሱ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በአየር ላይ እንዳሉ ተቀበላቸው፡፡ ብዕራቸው ግን መሬት ላይ ወድቃ ሸምበቆ ሆነች፡፡ ወዲያውም አባ ዮሐኒ ክንፍ አውጥተው ከቅዱስ ገብርኤል ጋር ጎን ለጎን ሆነው በዛሬው ዕለት ኅዳር 5 ቀን ወደ ብሔረ ሕያዋን ይዟቸው ገባ፡፡
ብሔረ ሕያዋን ያሉ እነ ሄኖክና ኤልያስም ‹‹ሰው ከሚሞትበት ሀገር ሞት ወደሌለበት አገር ማን አመጣው/›› አሉ፡፡ መልአኩም በዚህ ጊዜ እግዚአብሔር ባዘዘኝ ጊዜ እኔ ገብርኤል ነኝ ያመጣሁት›› አላቸው፡፡ ቀጥሎም መልአኩ ‹‹አንተ ሄኖክ ምንም ንጹሕ ብትሆን በሥርዓተ ሥጋ ተወልደህ በሥርዓተ ሥጋ አድገህ ሚስት አግብተህ ወልደሃል፣ እግዚአብሔርም እዚህ ያደረሰህ በንፅህናህ ነው፤ አንተም ኤልያስ ምንም ድንግል ብትሆን በሥርዓተ ሥጋ ተወልደህ በሥርዓተ ሥጋ አድገህ ከዚህ ደርሰሃል፤ ይህ አባ ዮሐኒ ግን ከተወለደ ጀምሮ የእናቱን ጡት አልቀመሰም፣ ቀን ቀን ሰሳ እያጠባችው ሌሊት ሌሊት ንስር አሞራ በክንፎቹ እያለበሰው አድጓል እንጂ›› ብሎ ነገራቸው፡፡ ቀጥሎም መልአኩ የአባ ዮሐኒን ገድል ዘርዝሮ ከነገራቸው በኋላ ሊሞት ያለበትንም የአሟሟቱን ነገር ከነገራቸው በኋላ ‹‹ታዲያስ እንዲህ ያለውን አምጥቼ ከብሔር ሕያዋን ባስገባው ፍርዴ እውነት አይደለምን?›› አላቸው፡፡ ሄኖክና ኤልያስም ይህን ጊዜ ‹‹ይገባዋል›› ብለው አባ ዮሐኒን በምስጋና ተቀበሉት፡፡
ከዚህም በኋላ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ወደ ደብረ ዓሣ ተመልሶ መጥቶ ለአባ አበይዶ ተገለጠላቸውና አባ ዮሐኒን ብሔረ ሕያዋን እንዳስገባው ነገራቸው፡፡ በመጀመሪያ ሄኖክና ኤልያስ አላስገባ ብለው እንደነበርና በኋላም መልአኩ ራሱ የአባ ዮሐኒን ገድላቸውን ከነገራቸው በኋላ በምስጋና እንደተቀበሉት ለአባ አበይዶ ነገራቸው፡፡ ቀጥሎም መልአኩ የአባ ዮሐኒን ገድላቸውን እንዲጽፉትና እንዲያስተምሩበት ለአባ አበይዶ አዘዛቸውና ዐረገ፡፡ አባ አበይዶም አባ ዮሐኒ ከገደሉ ተወርውረው ሲወደቁ አንድ ደስ የሚል ወንድ ሲቀበለው አይተው ነበርና አሁን መልአኩ ሲነግራቸው እጅግ ደስ አላቸው፡፡ አባ አበይዶም በታዘዙት መሠረት የአባ ዮሐኒን ገድል ጻፉት፡፡ እርሳቸውም ትናንት ኅዳር 4 ቀን በሰላም ዐረፉ፡፡
በፎቶው ላይ እንደምታዩት ተንቤን የሚገኘው የአባ ዮሐኒ ቤተ ክርስቲያን አቀማመጡ እጅግ አስደናቂ ነው፡፡ ተራራው መሀል ላይ ወደሚገኘው ቤተ ክርስቲያኑ ለመውጣት 150 ሜትር ተራራውን መውጣት ይጠይቃል፡፡ ሽቅብ ከተወጣ በኋላ አፈ ጽዮንን ትገኛለች፡፡ ከአፈ ጽዮን በኋላ ከድንጋይ የተፈለፈለ 12 መድረክ ያለው የውስጥ ለውስጥ የጨለማ መንገድ አለ፡፡ በመጨረሻ ብርሃን ወዳለብ ስፍራ ሲወጣ በስተግራ በኩል 12 ሜትር ርቀት ላይ ቤተ መቅዱሱ ይገኛል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ 13 ጉልላቶች አሉት፡፡ ገዳሙ ጥንት 58 ዓምደ ወርቅ ነበረው፡፡ በአንድ ወቅት በመሬት መንቀጥቀጥ ምክንያት 22ቱ ሲሰባበሩ አሁን ያሉት 36ቱ ብቻ ናቸው፡፡ ገዳሙ ውስጥ ሦስት ቤተ መቅደሶች ያሉ ሲሆን አንዱን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ይቀድሱበት የነበረው ነው፡፡ ገዳሙ ደብረ ዓሣ እየተባለ ይጠራል፡፡ ምክንያቱም ቤተ ክርስቲያኑ በመሬት መንቀጥቀጥ ከመፍረሱ በፊት ጣራው የዓሣ አንበሪ ቅርጽ ነበረው፡፡ ዐፄ ገብረ መስቀልም በወቅቱ በዚህ ዓሣ ምስል ያሠሩት ቅዱስ መስቀል በገዳሙ ውስጥ ይገኛል፡፡ አንድም ደግሞ በመጀመሪያ ዐፄ ገብረ መስቀል እና ሌሎቹም ቅዱሳን አበው በገዳሙ ውስጥ ሱባኤ ገብተው ሳለ ቅዱሳን በዓሣ ተመስለው ሲወጡና ሲገቡ በማየታቸው ነው ገዳሙ ‹‹ደብረ ዓሣ አባ ዮሐኑ›› የተባለው፡፡
ሌላው በተፈጥሮአዊ አቀማመጡ እጅግ ድንቅ በሆነው በዚህ ገዳም ውስጥ አስገራሚ የመቃብር ጉድጓዶች አሉት፡፡ መቃብሮቹ የጠፈለፈሉ ዋሻዎች ናቸው፡፡ አንዱ ዋሻ በአንድ ጊዜ ከ6 ሰዎችን ጎን ለጎን አስተኝቶ መያዝ አይችልም ነገር ግን በጣም የሚገርመው የመቃብር ጉድጓዶቹ እስከዛሬም ድረስ አልሞሉም፡፡ አንድ ሰው ከተቀበረ ከዓመት በኋላ አስክሬኑ ይጠፋል፣ አጥንቱም አይገኝም፡፡ ሰሌኑ ግን እስከ ሁለት ዓመት ይቀመጣል፡፡
ለአባ ዮሐኒ ለዚህ ገደማቸው ዕጣን ጧፍ ዘቢብ የሰጠ ሰው ቢኖር ስጦታውን እንደ አቤል መሥዋዕት አድርጎ ጌታችን እንደሚቀበልለት ለጻድቁ ቃልኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡
እግዚአብሔር ቢፈቅድ በዘንድሮው በ2008ቱ ለ16 ቀን ያህል በሚደረገው የኅዳሩ የአክሱም ጽዮን ጉዞአችን ላይ ከምንሳለማቸው ከ110 በላይ ገዳማትና አድባራት ውስጥ አንዱ ይህን እጅግ ድንቅ የሆነው የአቡነ ዮሐኒ ገዳም ነው፡፡

ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ይሁን! እኛንም በአማላጅነታቸው የምንታመን የተዋሕዶ ልጆች የሆንን ሁላችንን ዛሬ ኅዳር 1 ቀን በዓመታዊ በዓላቸው አስበናቸው የምንውለውን የአባ አሞኒን፣ የአባ ዮሐኒንና የአባ አበይዶንና የቅዱስ ሌንጊኖስን ረድኤት በረከታቸውን ያሳድርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን፡፡
(ከአባ ዮሐኒ ደብረ ዓሣ ገዳም የተገኙ ጽሑፎች፣ የጥቅምትና የሐምሌ ወር ስንክሳር፣ ቤተ ክርስቲያንህን ዕወቅ-ማኅበረ ቅዱሳን፣ ሐመር 13ኛ ዓመት ቁ.2 1997 ዓ.ም)